የክልሉ መንግስት ከህዝብ ጋር ተነጋግሮና ተወያይቶ እየሠራ ይገኛል – ዶ/ር ዲላሞ ኦቶሬ
ሀዋሳ: የካቲት 30/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መንግስት ዋና ተጠሪ ዶ/ር ዲላሞ ኦቶሬ የክልሉ መንግስት ከህዝብ ጋር ተነጋግሮና ተወያይቶ እየሠራ እንደሚገኝ ተናግረዋል::
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መንገዶች ባለሥልጣን ዱራሜ ዲስትሪክት ከሾኔ- አጀባ – ማዞሪያ ድረስ የተገነባው የ18 ኪ.ሜ የጠጠር መንገድ ተመርቋል::
በምረቃው መርሀግብር የተገኙት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መንግስት ዋና ተጠሪ ዶ/ር ዲላሞ ኦቶሬ የክልሉ መንግስት ከጅምሩ ህዝብን በልማት ጉዳይ ላይ በማወያየትና በማነጋገር እንዲሁም በማቀድ በጋራ እየሰራ ይገኛል ብለዋል::
መንገድ ወሳኝ የልማት አንቀሳቃሽ በመሆኑ ልዩ ትኩረት የተሰጠው ጉዳይ ነው ብለዋል::
የክልሉ መንግስት በቀጣይም በርካታ ህዝብን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የመሠረተ ልማት ሥራዎችን ከህዝብ ጋር ተቀራርቦ ይሠራል ያሉት ዶ/ር ዲላሞ ከሾኔ – አጀባ – ማዞሪያ ድረስ ያለው መንገድ በመጠናቀቁ ለአካባቢው ማህበረሰብ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል::
የተሠራውን መንገድ በአግባቡ መያዝ ከቻልን መንገዱ ለታለመለት አላማ እና ለረጅም ጊዜ አገልግሎት ሊሰጥ የሚችል ነው:: በመሆኑም ህብረተሰቡ ኃላፊነቱን እንዲወጣ ጥሪ አቅርበዋል::
በክልሉ የተጀመሩ ብዙዎቹ የመንገድ ፕሮጀክቶች ብዙ ሀብት የሚጠይቁ ናቸው ያሉት ደግሞ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የመሠረተ ልማት ክላስተር አስተባባሪና የትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር መሐመድ ኑሪዬ ናቸው::
ብዙ ሀብት የሚጠይቁ መሆናቸው ደግሞ በጊዜ ለማጠናቀቅ ፈተና ሆኗል:: በቀጣይ ግን በግባታ ሂደት ላይ ያሉትን ለማጠናቀቅ የክልል መንግስት ከፍተኛ ትኩረት መስጠቱን አስታውቀዋል::
የሀዲያ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማቲዎስ አኒዮ መንገዱ በሀዲያና እና ከምባታ ዞን ለሚኖሩ ዜጎች ኢኮኖሚያዊ እድገትና ለማህበራዊ መስተጋብር ትልቅ ፋይዳ ይኖረዋል ብለዋል::
ዛሬ የተመረቀው እና በ2014 ዓ.ም ግንባታው የተጀመረው ከሾኔ- አጀባ – ማዞሪያ ድረስ የተገነባው የ18 ኪ.ሜ የጠጠር መንገድ 18 ነጥብ 2 ሚሊዮን ብር ወጪ የተደረገበት መሆኑን በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መንገዶች ባለሥልጣን የዱራሜ ዲስትሪክት ሥራ አስኪያጅ ኢንጅነር ኃይሌ አበራ ተናግረዋል::
አጠቃላይ ወጪው በክልሉ መንግስት መሸፈኑንም ነው ያስታወቁት::
በምረቃ መርሀግብር የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መንግስት ዋና ተጠሪ ዶ/ር ዲላሞ ኦቶሬን ጨምሮ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የመሠረተ ልማት ክላስተር አስተባባሪና የትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር መሐመድ ኑሪዬ እና ሌሎችም የክልል፣ የዞንና የከተማ አስተዳደሩ የሥራ ኃላፊዎች በምልከታው ተገኝተዋል::
ዘጋቢ፡ ማሬ ቃጦ

More Stories
እየተከናወነ ያለውን የኮሪደር ልማት ሥራ ከዳር ለማድረስ በሚደረገው ርብርብ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሙዱላ ከተማ አስተዳደር ገለፀ
በትምህርት ሴክተር የመረጃ አያያዝ ውጤታማነት ዙሪያ በኩረት እየተሠራ መሆኑ ተገለጸ
ሁሉንም የመማሪያ መጻሕፍት ባለማግኘታቸው በትምህርታቸው ላይ ጫና እየፈጠረባቸው መሆኑን በጌዴኦ ዞን ይርጋጨፌ ወረዳ የቆንጋና ቆቄ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች ተናገሩ