የክልሉ መንግስት ከህዝብ ጋር ተነጋግሮና ተወያይቶ እየሠራ ይገኛል – ዶ/ር ዲላሞ ኦቶሬ
ሀዋሳ: የካቲት 30/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መንግስት ዋና ተጠሪ ዶ/ር ዲላሞ ኦቶሬ የክልሉ መንግስት ከህዝብ ጋር ተነጋግሮና ተወያይቶ እየሠራ እንደሚገኝ ተናግረዋል::
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መንገዶች ባለሥልጣን ዱራሜ ዲስትሪክት ከሾኔ- አጀባ – ማዞሪያ ድረስ የተገነባው የ18 ኪ.ሜ የጠጠር መንገድ ተመርቋል::
በምረቃው መርሀግብር የተገኙት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መንግስት ዋና ተጠሪ ዶ/ር ዲላሞ ኦቶሬ የክልሉ መንግስት ከጅምሩ ህዝብን በልማት ጉዳይ ላይ በማወያየትና በማነጋገር እንዲሁም በማቀድ በጋራ እየሰራ ይገኛል ብለዋል::
መንገድ ወሳኝ የልማት አንቀሳቃሽ በመሆኑ ልዩ ትኩረት የተሰጠው ጉዳይ ነው ብለዋል::
የክልሉ መንግስት በቀጣይም በርካታ ህዝብን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የመሠረተ ልማት ሥራዎችን ከህዝብ ጋር ተቀራርቦ ይሠራል ያሉት ዶ/ር ዲላሞ ከሾኔ – አጀባ – ማዞሪያ ድረስ ያለው መንገድ በመጠናቀቁ ለአካባቢው ማህበረሰብ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል::
የተሠራውን መንገድ በአግባቡ መያዝ ከቻልን መንገዱ ለታለመለት አላማ እና ለረጅም ጊዜ አገልግሎት ሊሰጥ የሚችል ነው:: በመሆኑም ህብረተሰቡ ኃላፊነቱን እንዲወጣ ጥሪ አቅርበዋል::
በክልሉ የተጀመሩ ብዙዎቹ የመንገድ ፕሮጀክቶች ብዙ ሀብት የሚጠይቁ ናቸው ያሉት ደግሞ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የመሠረተ ልማት ክላስተር አስተባባሪና የትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር መሐመድ ኑሪዬ ናቸው::
ብዙ ሀብት የሚጠይቁ መሆናቸው ደግሞ በጊዜ ለማጠናቀቅ ፈተና ሆኗል:: በቀጣይ ግን በግባታ ሂደት ላይ ያሉትን ለማጠናቀቅ የክልል መንግስት ከፍተኛ ትኩረት መስጠቱን አስታውቀዋል::
የሀዲያ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማቲዎስ አኒዮ መንገዱ በሀዲያና እና ከምባታ ዞን ለሚኖሩ ዜጎች ኢኮኖሚያዊ እድገትና ለማህበራዊ መስተጋብር ትልቅ ፋይዳ ይኖረዋል ብለዋል::
ዛሬ የተመረቀው እና በ2014 ዓ.ም ግንባታው የተጀመረው ከሾኔ- አጀባ – ማዞሪያ ድረስ የተገነባው የ18 ኪ.ሜ የጠጠር መንገድ 18 ነጥብ 2 ሚሊዮን ብር ወጪ የተደረገበት መሆኑን በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መንገዶች ባለሥልጣን የዱራሜ ዲስትሪክት ሥራ አስኪያጅ ኢንጅነር ኃይሌ አበራ ተናግረዋል::
አጠቃላይ ወጪው በክልሉ መንግስት መሸፈኑንም ነው ያስታወቁት::
በምረቃ መርሀግብር የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መንግስት ዋና ተጠሪ ዶ/ር ዲላሞ ኦቶሬን ጨምሮ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የመሠረተ ልማት ክላስተር አስተባባሪና የትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር መሐመድ ኑሪዬ እና ሌሎችም የክልል፣ የዞንና የከተማ አስተዳደሩ የሥራ ኃላፊዎች በምልከታው ተገኝተዋል::
ዘጋቢ፡ ማሬ ቃጦ
More Stories
የመልካም አስተዳደር ችግሮች ተቀርፈው ህብረተሰቡ ተገቢ አገልግሎት እንዲያገኝ መስራት እንደሚገባ ተገለጸ
በጉራጊኛ ቋንቋ የሚጻፉ መጽሐፍት ለቋንቋው እድገት፣ መልማት፣ መበልጸግና ወደ ትውልዱ ለማድረስ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አላቸው – ረዳት ፕሮፌሰር ካሚል ኑረዲን
የ”ባለ ካዳቤ” በዓል የዕርቅ፣ የፍቅር፣ የአንድነትና የብርሃን ተምሳሌት መሆኑ ተገለጸ