የትምህርትና ስልጠና ተቋማት ለሀገር ሁለንተናዊ ብልጽግና የማይተካ ሚና እንዳላቸው ተገለጸ
ሀዋሳ፡ የካቲት 30/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የትምህርትና ስልጠና ተቋማት ለሀገር ሁለንተናዊ ብልጽግና የማይተካ ሚና እንዳላቸው ተጠቁሟል፡፡
ጎታች አስተሳሰቦችን በመታገል፣ ለሰላም መስፈንና የህግ የበላይነት መከበር የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የድርሻቸውን ሊወጡ እንደሚገባ ተመላክቷል።
አቶሚክ ቴክኖሎጂና ቢዝነስ ኮሌጅ በሁለት የትምህርት መርሐግብሮች ለመጀመሪያ ዙር ያሰለጠናቸውን 118 የሁለተኛ ድግሪ ተማሪዎች አስመርቋል።
የኮሌጁ ፕረዚዳንት አቶ በፍቅሩ ተስፋዬ እንደገለጹት ኮሌጁ እውቅና ባገኘባቸው መስኮች ብቁና ተወዳዳሪ ዜጎችን ለማፍራት የትምህርት ሚኒስቴር ባስቀመጠው መስፈርት መሠረት የመማር ማስተማር ስነ-ዘዴን ተከትሎ ለመጀመሪያ ዙር በሁለት የትምህርት ዘርፎች ያሰለጠናቸውን 118 የሁለተኛ ድግሪ ተማሪዎችን ማስመረቃቸውን ተናግረዋል።
ኮሌጁ ከመማር ማስተማር ጎን ለጎን በምርምርና ማህበረሰብ አቀፍ አገልግሎት የአካባቢውን ህብረተሰብ ተጠቃሚ የሚያደርጉ ተግባራት በማከናወን አጋሪነቱን እየተወጣ ስለመሆኑንም ፕሬዚዳንቱ አቶ በፍቅሩ ተናግረዋል።
ተመራቂዎቹ ከኮሌጁ የቀሰሙትን እውቀት ማህበረሰቡን በቅንነትና በታማኝነት ማገልገል እንደሚጠበቅባቸው በፍቅሩ አመላክተዋል።
ህዝብና መንግስት ከተመራቂዎች ብዙ ይጠብቃል ያሉት ዶ/ር በፈቃዱ ከስራ ጠባቂነት በመላቀቅ በግልና በኢንተርፕራዝ በመደራጀት ለተጀመረው የብልጽግና ጉዞ አዎንታዊ አስተዋጽኦ ማበርከት እንደሚጠበቅባቸው ጠቁመዋል።
የእለቱ የክብር እንግዳና የሀዲያ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ ዶ/ር በፈቃዱ ወልደሀና በዚሁ ወቅት እንዳሉት የትምህርትና ስልጠና ተቋማት ለሀገር ሁለንተናዊ ብልጽግና የማይተካ ሚና ስላላቸው ለውጡን ወደ ኃላ ከሚጎትቱ አስተሳሰቦች በመላቀቅ ለሰላም መስፈንና ለህግ የበላይነት መከበር የድርሻቸውን ሊወጡ ይገባል ብለዋል።
ተመራቂዎችም በሰጡት አስተያየት በኮሌጁ ቆይታቸው በቀሰሙት እውቀት ማህበረሰቡን የበለጠ ለማገልገል ቁርጠኛ መሆናቸውን ተናግረዋል።
ዘጋቢ: ጡሚሶ ዳንኤል – ከሆሳዕና ጣቢያችን

More Stories
በ6 ወራት ውስጥ ሊመዘበር የነበረ ከ156 ሚሊየን 560ሺህ ብር በላይ ማዳን መቻሉ ተገለጸ
የጉራጌ ክትፎ ባህልና እውቀትን በዩኒስኮ የሰው ልጆች ወካይ የማይዳሰስ ቅርስነት ለማስመዝገብ እየተሰራ እንደሚገኝ የኢፌዲሪ ቅርስ ባለስልጣን ገለፀ
በክልሉ ያሉ ብሔረሰቦችን ባህል ወደፊት በማውጣት የአካባቢውን ሰላምና ልማት ለማስቀጠል በትኩረት መስራት እንደሚገባ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳደር ኢንጅነር ነጋሽ ዋጌሾ(ዶ/ር) ተናገሩ