በልማት ላይ በአርበኝነት መሥራት ይገባል – ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው

በልማት ላይ በአርበኝነት መሥራት ይገባል – ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው

ሀዋሳ: የካቲት 27/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው የተመራ የክልሉ አመራር በከምባታ ዞን አዲሎ ዙሪያ ወረዳ የግብርና ኢንቨስትመንት ልማት ሥራን ተመልክቷል::

በወረዳው በ10 ሄክታር መሬት ላይ በግብርና ኢንቨስትመንት ዘርፍ የለማውን የበጋ መስኖ ስንዴና የጓሮ አትክልት የተመለከቱት ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው አበረታች ሥራ ማየታቸውን ገልጸዋል::

በማሳው የታየውን መልካም ተሞክሮ በአቅራቢያ ባሉ አርሶ አደሮች እና በሌሎችም አካባቢዎች ማስፋት እንደሚገባ አንስተዋል::

አባቶቻችን በአርበኝነት ሀገርን ጠብቀው አስተላልፈውልናል ያሉት ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው እኛም በግብርና፣ በጤና በትምህርትና በሌሎችም መስኮች ለትውልድ የሚበቃ የአርበኝነት ሥራ መፈፀም ይጠበቅብናል ሲሉ ተናግረዋል::

ርዕሰ መስተዳድሩ የመስክ ምልከታው ዋና ዓላማ የግብርና እና የኢንቨስትመንት ሥራዎች ምን እንደሚመስሉ እንዲሁም ጥንካሬዎችን እና ጉድለቶችን በመስክ ላይ ለማየትና ተገቢውን ድጋፍ ለማድረግ ነው ብለዋል::

በከምባታ ዞን ተዘዋውረው የተመለከቷቸው በኢንዱስትሪው እና በግብርናው ረገድ የተከናወኑ ተግባራትም ተጠናክረው የሚቀጥሉ መሆናቸውን ገልጸዋል::

ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰውን ጨምሮ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪ እና የትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ አንተነህ ፍቃዱ፣ በብልፅግና ፓርቲ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ኃላፊ ዶ/ር ዲላሞ ኦቶሬ፣ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የገጠር ክላስተር አስተባባሪና የግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ኡስማን ሱሩር፣ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የመሠረተ ልማት ክላስተር አስተባባሪና የትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር መሐመድ ኑሪዬ እና ሌሎችም ከፍተኛ የክልሉ አመራሮች በመስክ ምልከታው ተሳትፈዋል::

ዘጋቢ፡ ማሬ ቃጦ