የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት ሁለተኛ መደበኛ ጉባኤውን ከመጋቢት 3 ጀምሮ ያካሂዳል

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት ሁለተኛ መደበኛ ጉባኤውን ከመጋቢት 3 ጀምሮ ያካሂዳል

ሀዋሳ፡ የካቲት 25/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የምክር ቤቱ ዋና አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፀሀይ ወራሳ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ምክር ቤቱ ከመጋቢት 3-6/2016 ድረስ በሚካሄደው በዚህ ጉባኤ በተለያዩ አጀንዳዎች ዙሪያ ይመክራል ተብሎ ይጠበቃል።

የክልል መንግስት የ6 ወራት ዕቅድ አፈፃፀም በምክር ቤቱ በዝርዝር የሚገመገም ሲሆን 19 አዳዲስ አዋጆች ይፀድቃሉ ተብሎ ይጠበቃል።

ዋና አፈ ጉባኤዋ የክልል ምክር ቤትና የፌዴራል የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት በአመት ሁለት ጊዜ ከመረጣቸው ህዝብ ጋር ውይይት እንደሚያደርጉ ጠቅሰው፥ በቅርቡ በየምርጫ ጣቢያቸው በመገኘት ከህብረተሰቡ ጋር ውይይት ማድረጋቸውን ገልጸዋል።

ከህብረተሰቡ ለተነሱ ጥያቄዎች፥ የህዝብ ተወካዮች ከመንግሥት አካላት ጋር ገንቢ ውይይት ማድረጋቸውን አስረድተዋል።

የህዝብ ጥያቄዎችን ለመመለስ የክልሉ መንግስት ያላሳለሰ ጥረት ያደርጋል ብለዋል።

የክልሉ መንግስት የህብረተሰቡን ሁለንተናዊ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ለመመለስ እየሰራ ነው ያሉት ወይዘሮ ፀሀይ፥ ለመንግሥት ውጥን መሳካት ህብረተሰቡ የነቃ ተሳትፎ እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል።

ዘጋቢ: ጀማል የሱፍ