በአባቶች አኩሪ ገድል የተገኘው የአድዋ ድል ድህነትን በማሸነፍና የሀገር ሰላምን በማስጠበቅ በአሁኑ ተውልድ ልደገም ይገባል – ወ/ሮ ፀሀይ ዳርጫ

በአባቶች አኩሪ ገድል የተገኘው የአድዋ ድል ድህነትን በማሸነፍና የሀገር ሰላምን በማስጠበቅ በአሁኑ ተውልድ ልደገም ይገባል – ወ/ሮ ፀሀይ ዳርጫ

ሀዋሳ፡ የካቲት 23/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ዳውሮ ዞን  128ኛ የአድዋ ድል በዓል በክልሉ ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት ቢሮ እና በዞኑ አዘጋጅነት በተለያዩ ክዋኔዎች በድምቀት ተከብሯል።

በክብረ በዓሉ የተገኙ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ ወ/ሮ ፀሀይ ዳርጫ በአባቶች አኩሪ ገድል የተገኘው የአድዋ ድል ድህነትን በማሸነፍና የሀገር ሰላምን በማስጠበቅ በአሁኑ ትውልድ ሊደገም ይገባል ብለዋል።

ምክትል አፈ ጉባኤዋ አክለውም ለመጪው ትውልድ የበለፀገች ሀገር ለማስረከብ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በአንድነት ሊቆም እንደሚገባም አሳስበዋል።

እንኳን ለ128ኛው የአድዋ ድል በዓል አደረሳችሁ ያሉት የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት ቢሮ ሀላፊ አቶ ፋንታሁ ብላቴ የአድዋ ድል መታሰቢያን በድምቀት የሚያሳይ የአድዋ ሙዚየም ተገንብቶ በተጠናቀቀበት ማግስት መሆኑ የዘንድሮውን በዓል ልዩ ያደርጋል ብለዋል።

ሀላፊው አክለውም ከፋፋይ አጀንዳዎችን በመተው ታላቋን ኢትዮጵያ ለመገንባት ዛሬ ላይ ያለው ትውልድ አርበኛ ልሆን እንደሚገባም አንስተዋል።

ለህብረብሔራዊ አንድነት፣ ለሰላምና ከደህነት ለመላቀቅ እንደ ሀገር እየተደረገ ባለው ርብርብ ሁሉም የበኩሉን አስተዋጽኦ ሊወጣ ይገባልም ብለዋል።

አቶ ፋንታሁን አክለውም የክልሉ ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት ቢሮ በአዲስ አበባ ተገንብቶ አገለግሎት መስጠት በጀመረው የአድዋ ድል መታሰቢያ ሙዚየም ውስጥ  ክልሉን የሚገልጽ የጀግንነት ቅርሶችን እንዳስቀመጠም አብራርተዋል።

የዳውሮ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ አስፋው ደሳለኝ በበኩላቸው እያንዳንዱ ዜጋ ከራስ በላይ ለሀገር ቅድሚያ በመስጠት በተሰማራበት የስራ መስክ ውጤታማ በመሆን የአድዋ ድልን መድገም ይገባል ብለዋል።

የአድዋ ድል በዓል የኢትዮጵያውያን የአሸናፊነት ስነ ልቦና በሚገባ የታየበት ደማቅ የአንድነት አሻራ እንደሆነም በመድረኩ ተነስቷል።

በበዓሉ የአድዋ ድልን የሚዘክር የተለያዩ የኪነ ጥበብ ስራዎችና ሰነዶች ቀርበዋል።

ዘጋቢ፡ አዲስዓለም ታዬ – ዋካ ጣቢያችን