የየም ዞን ምክር ቤት 5ኛ ዙር 9ኛ የሥራ ዘመን 2ኛ አስቸኳይ ጉባኤ መካሔድ ጀመረ

የየም ዞን ምክር ቤት 5ኛ ዙር 9ኛ የሥራ ዘመን 2ኛ አስቸኳይ ጉባኤ መካሔድ ጀመረ

ሀዋሳ፡ የካቲት 18/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የየም ዞን ምክር ቤት 5ኛ ዙር 9ኛ የሥራ ዘመን 2ኛ አስቸኳይ ጉባኤ መካሔድ ጀምሯል፡፡

ምክር ቤቱ በተለዩ ሁለት አጀንዳዎች ዙሪያ የመከረ ሲሆን፥ የ5ኛ ዙር 8ኛ የሥራ ዘመን 25ኛ መደበኛ ጉባኤ ቃለ-ጉባኤ፣ የ1ኛ አስቸኳይ ጉባኤ ቃለ ጉባኤ እና ልዩ ልዩ ሹመቶችን መርምሮ አጽድቋል።

ጉባኤውን በንግግር የከፈቱት የምክር ቤቱ ዋና አፈ ጉባኤ ዝናሽ ገ/ስላሴ፥ ምክር ቤቶች የህዝብ ሉዓላዊነት መገለጫ፣ በዲሞክራሲ ስርዓት ግንባታና በመንግሥት አሠራር ውስጥ የህዝብ ተሳትፎን በማረጋገጥ በህብረተሰቡ ኑሮ፣ መብትና  ነጻነት ላይ  አዎንታዊ ለውጥና መልካም አስተዳደር እንዲሰፍን የሚያደርጉ አውራ ተቋማት ናቸው ብለዋል።

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የብልጽግና ፓርቲ የፖለቲካና የአቅም ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ይሁን አሠፋ የዞኑን እጩ አስተዳዳሪ ለምክር ቤት አቅርበዋል።

በዚህ መሠረት የየም ዞን ዋና አስተዳዳሪ የነበሩትን አቶ ሳሙኤል ገ/ሚካኤል በማንሳት አቶ ሽመልስ እጅጉን ዋና አስተዳዳሪ አድርጎ ሾሟል።

ከዚህ በተጨማሪ አዲሱ የዞኑ አስተዳዳሪ ተጨማሪ እጩ ተሿሚዎችን ለምክር ቤቱ አቅርበዋል።

በዚህ መሠረት አቶ ገበየሁ ማሞ ኪያን ምክትል አስተዳዳሪና የሠላምና ጸጥታ መምሪያ ኃላፊ፣ ማዕረግ መኮንን የስራ ዕድል ፈጠራ ኤጀንሲ ኃላፊ እና ቴዎድሮስ ገዝሙን የመንግስት ኮሙኒኬሽን ኃላፊ አድርጎ ምክር ቤቱ በሙሉ ድምጽ ተቀብሎ አጽድቋል፡፡

ዘጋቢ፡ ዘላለም ተስፋዬ