በጤናው ዘርፍ የታዩ ስኬቶችን በተሻለ መልኩ ለማስቀጠል የጤና ባለሙያዎች የድርሻቸውን ሊወጡ እንደሚገባ የኢፌዴሪ ጤና ሚኒስቴር አስታወቀ

በጤናው ዘርፍ የታዩ ስኬቶችን በተሻለ መልኩ ለማስቀጠል የጤና ባለሙያዎች የድርሻቸውን ሊወጡ እንደሚገባ የኢፌዴሪ ጤና ሚኒስቴር አስታወቀ

የአርባምንጭ ዩኒቨርስቲ ለዘጠነኛ ጊዜ በህክምና መርሃ ግብር ያሰለጠናቸውን 70 የህክምና ዶክተሮችን በዛሬው እለት አስመርቋል።

ተመራቂ ዶክተሮችም በተማሩት የትምህርት ዘርፋ ማህበረሰቡን ለማገልገል መዘጋጀታቸውን ገልፀዋል።

የአርባ ምንጭ ዩኒቨርስቲ ለዘጠነኛ ጊዜ ያሰለጠናቸውን የህክምና ዶክተሮችን ባስመረቀበት ወቅት ተገኝተው ንግግር ያደረጉት የእለቱ ክብር እንግዳና የኢፌዴሪ ጤና ሚኒስቴር ልዩ አማካሪ ዶክተር ዳንኤል ገብረ ሚካኤል፤ ምንም እንኳ ሀገራችን በጤናዉ ዘርፍ ከፍተኛ ዉጤት እያስመዘገበች ያለች ቢሆንም ዛሬም ድረስ ቁጥራቸው አነስተኛ የማይባሉ የህብረተሰብ ክፍሎች በህክምና እጦት ሳቢያ እየተሰቃዩ መሆናቸውን ተናግረዋል።

ዛሬ የተመረቃችሁ ዶክተሮች የተሰጣችሁን የመንግስት እና የህዝብ ሀላፊነት በሚገባ በመወጣት ይጠበቅባችኋል ብለዋል ዶክተር ዳንኤል።

ዶክተሩ አክለውም ጊዜው የሚጠይቀዉን እዉቀት እና ክህሎት በተደራጀ መልኩ ለመጎናፀፍ ቀጣይነት ያለዉ ትምህርት ወሳኝ ነዉና ዕጩ ዶክተሮችም ሙያቸውን ለማሻሻል መትጋት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል።

የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶክተር ዳምጠዉ ዳርዛ በበኩላቸው ተመራቂ ዶክተሮች በሀገር አቀፍ ደረጃ የተሰጠውን የመዉጫ ፈተና በመውሰድ ሁሉም ተማሪዎች ማለፋቸው ዩኒቨርስቲው የትምህርት ጥራት ለማሻሻል እየሰራ መሆኑን የሚያሳይ ነው ብለዋል።

በሌሎች መስኮችም ተጨባጭ ለዉጦች እንዲመጡ እየሰራ ይገኛል ሲሉ ተናግረዋል።

እንደሀገር በአሁኑ ወቅት ከቅድመ መደበኛ አንስቶ እስከ ክፍተኛ ትምህርት ተቋማት ድረስ ሰፊ የለውጥ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን የገለፁት ዶክተር ዳምጠው፤ የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የትምህርት ምዘና፣ የትምህርት መሰረተ ልማት እና የቁሳቁስ ክፍተቶችን በሟሟላት አምራቾች እና ተወዳዳሪ የተማረ የሰው ሃይል ለማፍራት በትጋት እየሰራ ይገኛሉ ብለዋል።

ተመራቂ የህክምና ዶክተሮች በሀገራችንም ይሁን በዞናችን ዉስጥ ያለውን የህክምና ባለሙያዎች ቁጥር እጥረት ከማቃለል አኳያ ሚናቸው የጎላ መሆኑን ዶክተር ዳምጠው ጠቁመዋል።

በአሁኑ ጊዜ እየተበራከተ የመጣውን ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን ስርጭት ለመቀነስና ለመከላከል ጠንካራ ስራዎች ለመስራት ዩኒቨርሲቲው እያበረከተ ያለው እንቅስቃሴ ተሰፋ ሰጭ ዉጤቶች እየታዩ ነዉ ያሉት ደግሞ በዩኒቨርሲቲው ህክምናና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ ዳይሬክተር ዶክተር ደስታ ጋልቻ ናቸዉ።

ከተመራቂ ዶክተሮች መካከል ዶክተር ቅድስት አምታታዉ እና ዶክተር ዮሐንስ ስምዕን ሽብሩ ወደ ማህበረሰቡ ሲቀላቀሉ ሙያዊ ስነምግባር በተላበሰ መልኩ ለማገልገል መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።

የአርባ ምንጭ ህክምናና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ በሁለት ሺህ ዓመተ ምህረት ማስተማር የጀመረ ሲሆን የዛሬ ተመራቂዎችን ጨምሮ 755 የህክምና ዶክተሮች አስመርቋል።

ዩኒቨርስቲው በዛሬው ዕሌትም 70 የህክምና ዶክተሮችን ያስመረቀ ሲሆን ከእነዚህ መካከል 17ቱ ሴት የህክምና ዶክተሮች ናቸው፡፡

የሀገር ሽማግሌዎች ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎች፣ ተጋባዥ እንግዶች ታዳም ሆነዋል፡፡

ዘጋቢ፡ ደግሰው በቀለ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን