በክልሉ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች እንዲጠበቁ ሁሉም የሚጠበቅበትን ሊወጣ ይገባል – አቶ አክመል አህመዲን
ሀዋሳ: የካቲት 14/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በክልሉ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ተጠብቀው የህግ የበላይነት ይረጋገጥ ዘንድ ሁሉም የሚጠበቅበትን ሊወጣ እንደሚገባ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ፍትህ ቢሮ ኃላፊ አቶ አክመል አህመዲን አሳሰቡ::
የክልሉ ፍትህ ቢሮ የስድስት ወራት የሥራ ክንውኑን በየደረጃው ከሚገኙ የዘርፉ መዋቅርና ባለድርሻ አካላት ጋር በቡታጅራ ከተማ እየገመገመ ይገኛል::
ባለፉት ስድስት ወራት ቢሮው የክልሉን ህዝብ ጥቅም የማስጠበቅ፣ የህብረተሰቡን ንቃተ ህግ የማሳደግ፣ ወንጀል ፈጻሚዎች ለህግ እንዲቀርቡ እና ተጠያቂ እንዲሆኑ ማስቻሉን የግምገማ መድረኩን በንግግር የከፈቱት የቢሮው ኃላፊ አቶ አክመል አህመዲን ገልጸዋል::
ከቢሮው እስከታችኛው መዋቅር ድረስ በተለወጠ አመለካከትና አሰራር አገልግሎት አሰጣጡን ውጤታማ ለማድረግ የተሠራው ሥራ የተሟላ ባይሆንም አበረታች ውጤት ታይቶበታል ብለዋል::
በወንጀልና በፍትሀብሔር፣ በህግ ጥናት ማርቀቅና ማስረፅ፣ በሙስና ወንጀሎች፣ በጠበቆችና ሲቪክ ማህበራት ክትትል፣ በወንጀል ጉዳዮች፣ በክስ ዝግጅትና በችሎት ክርክር ከማዕከል እስከ ታችኛው መዋቅር በግማሽ አመቱ ወደተያዘው ግብ መድረስ የሚያስችል አፈፃፀም ተመዝግቧል::
የፍትህ አገልግሎት አሰጣጥን በማሻሻል በክልሉ መልካም አስተዳደር ማስፈንና ከህዝብ የሚነሱ እሮሮዎችን ለመቀነስ በጅምር ላይ ያለ ተግባር ቢኖርም በቀጣይ ልዩ ጥረትና ቁርጠኝነትን የሚጠይቅ መሆኑን ኃላፊው ገልጸዋል::
መድረኩ በተመዘገቡ ውጤቶች ላይ ትኩረት ከማድረግ ይልቅ ወቅቱ የሚጠይቀውንና የህዝባችንን አዳጊ ፍላጎት ማዕከል በማድረግ ክፍተቶቻችንን ለይተን ለተሻለ አፈፃፀም ለማምጣት በሚያስችል መልኩ ውይይት የሚደረግበት ነው ብለዋል::
በክልሉ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ተጠብቀው የህግ የበላይነት ይረጋገጥ ዘንድ ሁሉም የሚጠበቅበትን ሊወጣ እንደሚገባም ነው አቶ አክመል ያሳሰቡት::
በግምገማ መድረኩ የፍትህ ዘርፍ ተጠሪ ተቋማት አመራሮች እና የክልል፣ የዞንና ልዩ ወረዳ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል::
ዘጋቢ፡ ማሬ ቃጦ

More Stories
የሰራተኞች የገንዘብ ቁጠባ እና ብድር ኅብረት ሥራ ማህበር ብዙዎችን የቤት ባለቤት ማድረጉ ተገለጸ
በሁሉም ዘርፎች እንደሀገር አመርቂ ውጤቶች እየተዘመገቡ ነው – የቦንጋ ከተማ ነዋሪዎች
የወሳኝ ኩነት ምዝገባ ስርዓትን በማዘመን የመረጃ ታማኝነትን ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑ ተገለጸ