በክልሉ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች እንዲጠበቁ ሁሉም የሚጠበቅበትን ሊወጣ ይገባል – አቶ አክመል አህመዲን
ሀዋሳ: የካቲት 14/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በክልሉ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ተጠብቀው የህግ የበላይነት ይረጋገጥ ዘንድ ሁሉም የሚጠበቅበትን ሊወጣ እንደሚገባ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ፍትህ ቢሮ ኃላፊ አቶ አክመል አህመዲን አሳሰቡ::
የክልሉ ፍትህ ቢሮ የስድስት ወራት የሥራ ክንውኑን በየደረጃው ከሚገኙ የዘርፉ መዋቅርና ባለድርሻ አካላት ጋር በቡታጅራ ከተማ እየገመገመ ይገኛል::
ባለፉት ስድስት ወራት ቢሮው የክልሉን ህዝብ ጥቅም የማስጠበቅ፣ የህብረተሰቡን ንቃተ ህግ የማሳደግ፣ ወንጀል ፈጻሚዎች ለህግ እንዲቀርቡ እና ተጠያቂ እንዲሆኑ ማስቻሉን የግምገማ መድረኩን በንግግር የከፈቱት የቢሮው ኃላፊ አቶ አክመል አህመዲን ገልጸዋል::
ከቢሮው እስከታችኛው መዋቅር ድረስ በተለወጠ አመለካከትና አሰራር አገልግሎት አሰጣጡን ውጤታማ ለማድረግ የተሠራው ሥራ የተሟላ ባይሆንም አበረታች ውጤት ታይቶበታል ብለዋል::
በወንጀልና በፍትሀብሔር፣ በህግ ጥናት ማርቀቅና ማስረፅ፣ በሙስና ወንጀሎች፣ በጠበቆችና ሲቪክ ማህበራት ክትትል፣ በወንጀል ጉዳዮች፣ በክስ ዝግጅትና በችሎት ክርክር ከማዕከል እስከ ታችኛው መዋቅር በግማሽ አመቱ ወደተያዘው ግብ መድረስ የሚያስችል አፈፃፀም ተመዝግቧል::
የፍትህ አገልግሎት አሰጣጥን በማሻሻል በክልሉ መልካም አስተዳደር ማስፈንና ከህዝብ የሚነሱ እሮሮዎችን ለመቀነስ በጅምር ላይ ያለ ተግባር ቢኖርም በቀጣይ ልዩ ጥረትና ቁርጠኝነትን የሚጠይቅ መሆኑን ኃላፊው ገልጸዋል::
መድረኩ በተመዘገቡ ውጤቶች ላይ ትኩረት ከማድረግ ይልቅ ወቅቱ የሚጠይቀውንና የህዝባችንን አዳጊ ፍላጎት ማዕከል በማድረግ ክፍተቶቻችንን ለይተን ለተሻለ አፈፃፀም ለማምጣት በሚያስችል መልኩ ውይይት የሚደረግበት ነው ብለዋል::
በክልሉ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ተጠብቀው የህግ የበላይነት ይረጋገጥ ዘንድ ሁሉም የሚጠበቅበትን ሊወጣ እንደሚገባም ነው አቶ አክመል ያሳሰቡት::
በግምገማ መድረኩ የፍትህ ዘርፍ ተጠሪ ተቋማት አመራሮች እና የክልል፣ የዞንና ልዩ ወረዳ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል::
ዘጋቢ፡ ማሬ ቃጦ

More Stories
የህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት የ2018 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸምና የ2019 ጠቋሚ ዕቅድ ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር እየመከረ ነው
የጠምባሮ ልዩ ወረዳ አርሶ አደሮች የመኸር እርሻ የማሳ ዝግጅት ቢያደርጉም በቂ ግብዓት አለማግኘታቸውን ገለጹ
ፋይዳ ብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ የህዝብና የመንግስት አገልግሎቶችን የሚያፋጥን በመሆኑ ለሁሉም ለማድረስ በትኩረት እየተሰራ መሆኑ ተገለጸ