በእውቀት ና ክህሎት የበለጸገ ዜጋን ለማፍራት ሁሉም ባለድርሻ አካላት የበኩላቸውን ሚና መወጣት ይጠበቅባቸዋል – አቶ አንተነህ ፍቃዱ

ሀዋሳ፡ የካቲት 11/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በጉራጌ ዞን እኖር ወረዳ  “አንድ መጽሐፍ ለአንድ ተማሪ” በሚል መሪ ቃል በተሰራው የንቅናቄ ስራ ታትመው የገቡ ከ 1 ኛ እስከ 6 ኛ ክፍል የመማሪያ መጽሐፍ ለተማሪ ማሰራጫ መርሃ ግብር እየተደረገ ይገኛል።

በመርሃ ግብሩ ላይ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር እና የትምህርት ቢሮ ኃላፊ፣ የትምህርት ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ አስከብር ወልዴን የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ለጫ ጋሩማን ጨምሮ ከፍተኛ የክልል፣ የዞንና የወረዳ አመራሮች ተገኝተዋል።

በዚሁ መድረክ ላይ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ አንተነህ ፍቃዱ የገጠመንን የትምህርት ብልሽት ለማስተካከል አዲስ የትምህርት ፍኖተ ካርታ መዘጋጀቱን በመጠቆም ፍኖተ ካርታው ተማሪዎችን በምርምር ና ፈጠራ ስራዎች ላይ ትኩረት እንዲያደርጉ የሚያግዝ እንደሆነ ተናግረዋል።

እንደ ክልል የትምህርት ጥራቱን ለማሳካት የመጽሐፍ አቅርቦት ትልቁን ሚና ይወጣል ያሉት አቶ አንተነህ በክልል ደረጃ ስድስት መቶ ሚሊየን ብር ለዚህ ተግባር ያስፈልጋል በማለት ሁሉም ዞኖችና ወረዳዎችን ጭምር ከተማ አስተዳደሮችም የበኩላቸውን ሚና እየተወጡ እንዳለ በመናገር በዛሬው ዕለት በጉራጌ ዞን እኖር ወረዳ  “አንድ መጽሐፍ ለአንድ ተማሪ” በሚል መሪ ቃል በተሰራው የንቅናቄ ስራ ታትመው የገቡ ከ 1 ኛ እስከ 6 ኛ ክፍል  የመማሪያ መጽሐፍ ርክክብ ተደርጓል።

መጽሐፍቶቹ በአጠቃላይ በወረዳው አማካይነት ከ 8 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ ተደርጎ ህትመት እንደተፈጸመ ተናግረዋል።

ትምህርትን ለፈጠራ መጠቀም ከተቻለ በርካታ ስራ ፈጣሪዎች መፍጠር እንደሚቻል አንስተዋል።

የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ለጫ ጋሩማ በበኩላቸው የትምህርት ጥራት ተደራሽነትን ለማስፋት መምህራንን ከማሰልጠን ጎንለጎን መጽሐፍ አንድ መጽሐፍ ለ 4 እና 5 ተማሪዎች በማዳረስ ያሉ የመማር ማስተማር ስራዎችን ችግሩ ሙሉ ለሙሉ እስኪቀረፍ ያሉ አማራጮችን እንሞክራለን ብለዋል።

የእኖር ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ መብራቴ ተክሌ በበኩላቸው ዛሬ ለመማሪያነት የተገዙ መጽሐፍት ከመንግሥት፣ ከአርሶ ከደሩና ከማህበረሰብ ክፍል በተሰበሰበ ገንዘብ ነው ያሉ ሲሆን ለመማር ማስተማር ስራው ውጤታማነት የህብረተሰቡ ተሳፎ ወሳኝ እንደሆነ አክለዋል።

ያነጋገርናቸው መምህራንና የተማሪ ወላጆችም ዛሬ የተደረገው የመጽሐፍ ርክክብ ለትምህርት ጥራቱ ቀላል የማይባል ሚና ይወጣል ሲሉ ገልጸዋል።

በተጨማሪም ከዚህ ቀደም ተማሪዎች በመጽሐፍ እጥረት ምክንያት ያጡ የነበረውን እውቀት ለመከለስ እንደሚችሉ አስታውሰዋል።

በመጨረሻም አቶ አንተነህና ሌሎች አመራሮች በወረዳው በአለማየሁ ከተማ የመንገድ ስራዎችን ኮንስትራክሽን ድርጅት አማካይነት ከ 32 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ ይደረግበታል የተባለውን የጋምቦ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤትንም ጎብኝተዋል።

ዘጋቢ፡ ብሩክ አማረ