የምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ ፕሮጀክት /FSRP/ ለቀጣይ 7 ዓመታት በግብርናው ዘርፍ በሚያከናውናቸው ተግባራት ዙሪያ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት አካሂዷል

ሀዋሳ፡ የካቲት 11/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በማዕከላዊ አትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ የምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ ፕሮጀክት አስተባባሪ አቶ ከድር መሐመድ እንደገለፁት፤ ከዚህ ቀደም የነበረው የግብርና እድገት ፕሮግራም/AGP/ በክልሉ ባለፉት ዓመታት በአንስተኛ መስኖ ልማት፣ በተፈጥሮ ሀብት ልማት ጥበቃ ስራ፣ በገበያ ተደራሽነትና በሌሎች የግብርና ስራዎችን በመፈጸም የክልሉን ህዝብ ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል።

የግብርና እድገት ፕሮግራም/AGP/ የተለያዩ ውጤቶችን በማምጣትና የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት በማረጋገጡ በተሻለ መንገድ የምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ ፕሮጀክት/FSRP/  በሚል ስያሜ ለሚቀጥሉት 7 ዓመታት አዳዲስ የግብርና አገልግሎቶችን በማሻሻል፣ የአንስተኛ መስኖ ልማት መገንባት እና በገበያ መሠረተ ልማት ዙሪያ ትኩረት ሰጥቶ ይሰራል ብለዋል።

በግብርናው ዘርፍ የተከናወኑ ልማቶችን አጠናክሮ ማስቀጠልና ማህበረሰቡን ተጠቃሚ በሚያደርጉ በሰብል ልማት፣ በ30 40 30 የአትክልትና ፍራፍሬ፣ በእንሰት፣ ቅመማ ቅመም እና በሌሎች ዘርፎች ይሰራሉ ያሉት አቶ ከድር፤ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በሚሰሩ ተግባራት ውስጥ አጋዥ ሆኖ እንደሚቀጥል ጠቁመዋል።

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ ተወካይና የግብርና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ አህመድ ሀቢብ በበኩላቸው፥ የምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ ፕሮጀክት /FSRP/  የመንግስት ክፍተት ያለባቸውን የግብርና ተግባራትን መደገፍና ማሟላት መሆኑን አመላክተዋል።

የፕሮግራሙን ግብ ለማሳካት በየደረጃ ያለው አካል ኃላፊነት አለበት ያሉት አቶ አህመድ፤ ፕሮጀክቱ ቅድሚያ የሚሰጠውን ተግባር እንደየአካባቢው ተጨባጭ ሁኔታ በግልፅ እቅድ ታቅዶ ወደ ስራ መግባት ይገባል ብለዋል።

የምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ ፕሮጀክት /FSRP/ የተሻለ እና ማህበረሰቡን ለበለጠ ተጠቃሚ ለማድረግ የቀድሞ ግብርና እድገት ፕሮግራም AGP/ ውጤት መሆኑን ጠቁመው፤ የምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ ፕሮግራም የክልሉን ህዝብ  የተሻለ ምርት በማምረት የአመጋገብ ስርዓት እንዲያሻሽል የሚሰራ በመሆኑ፤ ለህዝቡ ባለቤትነት መስራት ይገባል ብለዋል።

ፕሮጀክቱ በሰው ህይወት ላይ ለውጥ ለማምጣት አላማ ይዞ የመጣ በመሆኑ በግብርና እድገት ፕሮግራም/AGP/ ያልተከናወኑ ተግባራት እና በምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ ፕሮጀክት፤ የተቀመጡ ግቦችን በአግባቡ ለመፈፀም በቅድሚያ ሊያሰራ የሚችል እቅድ መታቀድ ይገባል ብለዋል።

ማህበረሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ በየደረጃው የግንዛቤ ፈጠራ፣ ድጋፍና ክትትል እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል።

ዘጋቢ፡ ዘላለም ተስፋዬ