በሀላባ ዞን ቁሊቶ ከተማ አስተዳደር ”ከዕዳ ወደ ምንዳ” በሚል መሪ ቃል ህዝባዊ የውይይት መድረክ እየተካሄደ ነው

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ፍትህ ቢሮ ሀላፊ አቶ አክመል አህመድ፣ የሐላባ ዞን ዋና አስተዳዳሪ  አቶ ሙህዲን ሁሴን፣ የሀላባ ዞን ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ሀላፊ አቶ መሐመድ ከማል ኑርዬ የክልልና የዞኑ ከፍተኛ አመራሮች በህዝባዊ የውይይት መድረኩ ታድመዋል።

ከከተማው የተውጣጡ የንግዱ ማህበረሰብ ተወካዮች፣ የሀይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የወጣት አደረጃጀቶች እና ልዩ ልዩ የህብረተሰብ ክፍሎችም በመርሐ ግብሩ እየተሳተፉ ናቸው።

በከተማው የተከናወኑ የልማትና የመልካም አስተዳደር ተግባራት ለውይይቱ መነሻ ጽሑፍ ያቀረቡት የሐላባ ቁሊቶ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ገመዳ መሐመድ ከተማዋ በፈርጅ ሁለት የምትመደብ መሆኑን አንስተው በየወቅቱ በምታሳየው ፈጣን እድገት በየጊዜው የፕላን ማሻሻያ እንዲደረግ አስገድዷል ብለዋል።

ከሀገራዊ ለውጡ ወዲህ በተመዘገበው ሁለንተናዊ ለውጥ በቁሊቶ ከተማ ዙሪያ ያሉ 7 ቀበሌያትን ወደ ከተማው በማካለል አዲስ ኘላን ገቢራዊ ተደርጓል ነው ያሉት።

በኢንቨስትመንት ስም መሬት ወስደው ባላለሙ አካላት ላይ ከ1 ነጥብ 2 ሄክታር በላይ መሬት ወደ መሬት ባንክ ተመልሷል ብለዋል።

በከተማው የመንገድ ከፈታ መደረጉን የጠቀሱት ከንቲባው የከተማው ህዝብም ለዚህ የሚሆን ከ400 ሚሊዮን ብር በላይ አስተዋጽኦ አበርክቷል ነው ያሉት።

የክልሉ ፍትህ ቢሮ ሀላፊ አቶ አክመል አህመድ ኢትዮጵያ ሊለማ የሚችል መሬት፣ ንጹህ አየር ፣ አመቱን ሙሉ የሚፈስ የውሀ ሐብት ታይተው የማይጠገቡ የቱሪስት ሀብቶችና የድንቅ ባህል እና እሴቶች ባለቤት ናት ብለዋል።

እነዚህን ሀብቶችን በመጠቀም ሀብት መፍጠርና የብልጽግና ጉዞን ማረጋገጥ አለብን ብለዋል።

ዘጋቢ: አብደላ በድሩ