በጂንካ ከተማ አስተዳደር ጽ/ቤት አስተባባሪነት የተዘጋጀ ክልላዊ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ዓመታዊ ማስጀመሪያ መርሃ-ግብር ተካሄደ

በጂንካ ከተማ አስተዳደር ጽ/ቤት አስተባባሪነት የተዘጋጀ ክልላዊ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ዓመታዊ ማስጀመሪያ መርሃ-ግብር ተካሄደ

ሀዋሳ፡ ህዳር 01/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ወጣቶቸና ስፖርት ቢሮ በአሪ ዞን ወጣቶችና ስፖርት መምሪያ በጂንካ ከተማ አስተዳደር ጽ/ቤት አስተባባሪነት የተዘጋጀ ክልላዊ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ዓመታዊ ማስጀመሪያ መርሃ-ግብር ተካሄደ።

በአካል ብቃት እንቅስቃሴው የከተማውና አካባቢው ማህብረሰብ ተሳትፈዋል።

በአካል ብቃት እንቅስቃሴው የተገኙት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ምክትልና ሚዲያና የህዝብ ግንኙነት ዘርፍ ሀላፊ አቶ ደለለኝ ሀብታሙ እንደገለፁት፤ የአካል እንቅስቃሴ ተግባራት ለሰው ልጅ ዘርፈብዙ ጠቀሜታ አላቸው።

ክልሉ ይህንን የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ሥራውን ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመቀናጀት አጠናክሮ ለማስቀጠል ማስጀመሪያ መርሃ-ግብሩ መካሄዱንም ሀላፊው አስረድተዋል።

የክልሉ ጤና ቢሮ የቤተሰብ ዕቅድና የአፍላ ወጣቶች ጤና ባለሙያ አቶ አብርሃም ወንድሙ እንዳሉት፤ የአካል ብቃት እንቅስቃሴዎች በየትኛውም የዕድሜ ክልል ላለ ሰው በሁሉ አቀፍ ጤና ዘርፍ እጅግ በርካታ ጠቀሜታዎች አሉት።

የአሪ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብርሃም አታ እና የጂንካ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ አስፋው ዶሬ በጋራ እንደገለፁት፤ የአካል ብቃት እንቅስቃሴዎች ከጤና ጥቅሞች ባሻገር የህዝቦች ትስሰርን በማጠናከር ለወዳጅነት፣ ለአብሮነትና ለፍቅር ትልቅ ጉልበት ያላቸው በመሆኑ መላው ህዝብ በዚህ ተሳታፊ እንዲሆን ጥሪ አቅርበዋል።

ከአንድ ወር በኋላ የአሪ ብሔረሰብ ድሽታ ግና የዘመን መለወጫ ክብረ በዓል የሚከበር ሲሆን እስከ በዓሉ ድረስ የተለያዩ ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎችን ለማካሄድ ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን ገልፀዋል የሥራ ኃላፊዎቹ።

በዓሉ የፍቅር፣ የሰላምና የአንድነት ሆኖ ደምቆ እንዲከበር በስፖርታዊ እንቅስቃሴዎች ሁሉም በመሳተፍ የድርሻውን እንዲወጣም ጥሪ አቅርበዋል።

የአካል ብቃት እንቅስቃሴው የተሳተፉ አካላትም ለተሻለ ጤናና ወዳጅነት አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስተያየታቸውን ገልፀዋል።

ዘጋቢ: ተመስገን አበራ – ከጂንካ ጣቢያችን