ጳጉሜ 02 ቀን የመስዋዕትነት ቀን በፓናል ዉይይትና መስዋዕትነት ለከፈሉ ለጸጥታ ኃይሎች ዕዉቅና በመስጠት እየተከበረ ነው – የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ፖሊስ ኮሚሽን

ጳጉሜ 02 ቀን የመስዋዕትነት ቀን በፓናል ዉይይትና መስዋዕትነት ለከፈሉ ለጸጥታ ኃይሎች ዕዉቅና በመስጠት እየተከበረ ነው – የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ፖሊስ ኮሚሽን

ሀዋሳ፡ ጳጉሜ 02/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) ጳጉሜን 02 ቀን የመስዋዕትነት ቀን በፓናል ዉይይትና መስዋዕትነት ለከፈሉ ለጸጥታ ኃይሎች ዕዉቅና በመስጠት እየተከበረ መሆኑን የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ።

ኮሚሽኑ ሀገርን ለማስቀጠል መስዋዕት ለከፈሉ የጸጥታ ኃይሎች የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፏል።

ዕለቱን አስመልክቶ መልዕክት ያስተላለፉት የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ሰብስቤ ሻዎኖ እንደገለጹት የሀገር አንድነትና ሉዓላዊነትን ለማስከበር ራሳቸዉን አሳልፈዉ የሰጡ የጸጥታ ሁይሎች የሚዘከሩበትና ዕዉቅና የሚቸራቸዉ ይሆናል ብለዋል።

ኢትዮጵያ እንደ ሀገር ለመቀጠል ችግር ዉስጥ በገባችበት ወቅት ከዚሁ ችግር ለማላቀቅ በተደረገዉ ትግል የክልሉ የጸጥታ ኃይሎች የከፈሉት ዋጋ በገንዘብም የማይተመን ከባድ መስዋዕትነት መሆኑን ጠቁመዋል።

ከዚህም በተጨማሪ በክልሉ በተለያዩ አባቢዎች የተፈጠሩ ችግሮችን በመፍታት አንጻራዊ ሰላም እንዲሰፍን በክልሉ በሁሉም መዋቅሮች የሚገኙ የጸጥታ ኃይሎች ሚና የጎላ እንደነበረም ኮሚሽነሩ  አስታዉሰዋል።

ቀኑ በክልሉ በሁሉም አካባቢዎች በሚገኙ መዋቅሮች የፓናል ዉይይት በማድረግ ሀገርን ለማስቀጠል መስዋዕትነት የከፈሉ የጸጥታ አካላትን በመዘከርና ዕዉቅና ይሰጣል ብለዋል ኮሚሽነር ሰብስቤ።

በመጨረሻም መላዉን የክልሉን ጸጥታ አካላትና ህዝብ እንኳን ለመስዋዕትነት ቀን በሰላም አደረሳችሁ ሲሉ የመልካም ምኞት መልዕክት አስተላልፈዋል።

 ዘጋቢ፡  አሰግድ ሣህሌ – ከቦንጋ ጣቢያችን