የቅጠል ቡና (ሀይታ ቱኬ)

የቅጠል ቡና (ሀይታ ቱኬ)

በወላይትኛ “ሀይታ ቱኬ” ወይም የቅጠል ቡና በመባል የሚታወቀው በተለያዩ አካባቢዎች እንደ ቡና እና ሻይ ተዘውትሮ የሚጠጣ ባህላዊ ትኩስ የመጠጥ አይነት ነዉ።

ታዲያ ሀይታ ቱኬን ለማዘጋጀት እርጥብ የቡና ቅጠል፣ በሶብላ፣ ድምብላል፣ ነጭ ሽንኩርት፣ የጠጅ ሳር፣ አርቲ፣ ጤና አዳም፣ ዝንጅብል መሆናቸውን በወላይታ ሶዶ የቅጠል ቡና አዘጋጇ ወ/ሪት መሠረት ዘሪሁን ታስረዳለች፡፡

መጀመሪያ እርጥብ የቅጠል ቡና ተለቅሞ ከተወቀጠ በኋላ ፀሀይ ላይ እንዲደርቅ ይደረጋል፡፡ ከዚያም የሚበቃውን ያክል ዉሃ ተመጥኖ ይጨመርና ከፈላ በኋላ የቡናዉን ዉሃ እንዲጠል በማድረግ አንድ ላይ ከተወቀጡት ቅመማ ቅመሞች ጋር በማፍላት ለመጠጥነት ዝግጁ እንደሚሆን ታብራራለች።

የቅጠል ቡናው እንደየተጠቃሚው ምርጫ ለምግብነት ከተዘጋጀ ድንች፣ቦሎቄ፣ ቦዬ፣ ቦይና፣ እሸት በቆሎ፣ እና ከዳጣ ጋር ይቀርባል፡፡

ሀይታ ቱኬ ወይም የቅጠል ቡና በማንኛውም የዕድሜ ክልል ዉስጥ ያሉ ሰዎች የሚጠቀሙት ሲሆን ለጉፋን፣ ለብርድ፣ በቅዝቃዜ ወቅት ሙቀት ለማግኘት ፍቱን መሆኑ ይነገራል።

ሀይታ ቱኬ ቤተሰብ ወይም ጎረቤት ሰብሰብ ባሉበት ተዘጋጅቶ ከቁርስ ጋር በደራ ጨዋታው መካከል ወዳጅነትን የሚያደራጅ  ባህላዊ ትኩስ መጠጥ ነው።

ወ/ሪት መሠረት ዘሪሁን እንዳሉት ወላይታ በእንግድነት ጎራ የሚሉ ሁሉ መንገድ ዳር ካሉ ምግቦች ጋር ከሚዘወተሩት ትኩስ መጠጦች ውስጥ ሀይታቱኬን እንዲቀምሱ በአስተያየታቸው ጠቁመዋል።

አዘጋጅ፡ ሐና በቀለ