በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ሁሉም ዜጋ በደም ልገሳ ተግባር ሊሳተፍ እንደሚገባ ጥሪ ቀረበ
ሀዋሳ፡ ሐምሌ 21/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ሁሉም ዜጋ በደም ልገሳ ተግባር ሊሳተፍ እንደሚገባ የአርባምንጭ ደም ባንክ ጥሪ አቅርቧል።
የክረምት በጎ ስራን ምክንያት በማድረግ በባስኬቶ ልዩ ወረዳ የደም ልገሳ መርሐ ግብር ተከናውኗል።
በደም ልገሳ ላይ የተሳተፉት የላስካ ከተማ ነዋሪዎች በሰጡት አስተያየት፥ በደም እጦት ህይወታቸውን የሚያጡ እናቶችን ሞት ለመቀነስ በሚደረገው ጥረት ውስጥ ሁሉም በደም ልገሳው በመሳተፍ የበኩሉን እንዲወጣ ጥሪ አቅርበዋል።
የአርባምንጭ ደም ባንክ ኃላፊ አቶ ታገል ጌታቸው በክረምት ወራት አብዛኛዎቹ ትምህርት ተቋማት መዘጋትን ተከትሎ በሚካሔዱ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት፥ የጤና ተቋማት የደም ፍላጎት ለማሟላት የተለያዩ ስራዎችን በማከናወን ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል።
አቶ ታገል አክለውም በክረምት በጎ ተግባር በየአካባቢው ለሚከናወነው የደም ልገሳ ሁሉም ዜጋ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ጠቁመዋል።
በባስኬቶ ልዩ ወረዳ በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት 120 ዩኒት ደም ለማሰባሰብ መታቀዱን የልዩ ወረዳው ወጣቶችና ስፖርት ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ መርዕድ ወንዱ ገልጸዋል።
በእለቱ ከአርባምንጭ ደም ባንክ ከላስካ መጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ጋር በመተባበር በጎ ፍቃደኛ ግለሰቦችን በማሳተፍ 80 ዩኒት ደም መሰብሰብ መቻሉንም ተናግረዋል።
የግልና አካባቢ ንጽህና ዙሪያ ግንዛቤ ማስጨበጥ፣ አምቡላስ በማይገባባቸው አካባቢዎች የህክምና የክትባት ቁሳቁሶችን ማጓጓዝና ሌሎችንም ተግባራት በቀጣይ አስከ ክረምቱ ማገባደጃ እንደሚከናወኑ አቶ መርዕድ አክለው አብራርተዋል።
ዘጋቢ: አወል ከድር – ከሳውላ ጣቢያችን

More Stories
ከመማር ማስተማር ተግባር ባለፈ የአካባቢ ማህበረሰብ ተጠቃሚነት ላይ ትኩረት አድርጎ እየሰራ መሆኑን የሚዛን ግብርና ቴክኒክ ሙያ ትምህርትና ስልጠና ኮሌጅ አስታወቀ
የኢፌዲሪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ(ዶ/ር) መጭው ጊዜ ከተስፋ ብርሃን ወደሚጨበጥ ብርሃን የምንሸጋገርበት ብሩህ ዘመን መሆኑን ተናገሩ
በተቀሩት አጭር ቀናት ህብረተሠቡ የመራጭነት ካርዱን በመውሰድ የዜግነት ግዴታውን እንዲወጣ የጎፋ ዞን መሎ ኮዛ ወረዳና አካባቢው የፌደራልና የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከፍተኛ አመራሮች ጥሪ አቀረቡ