የተጀመረውን ሪፎርም ሁሉም ባለድርሻ አካላት እንዲደግፉ ጥሪ ቀረበ

የተጀመረውን ሪፎርም ሁሉም ባለድርሻ አካላት እንዲደግፉ ጥሪ ቀረበ

ሀዋሳ፡ ሐምሌ 15/2015 ዓ.ም (ደሬቴድ) የትምህርት ቤቶችን መሠረተ ልማት ለማሻሻል የተጀመረውን ሪፎርም ሁሉም ባለድርሻ አካላት እንዲደግፉ ጥሪ ቀረበ።

በጎፋ ዞን የትምህርት ቤቶችን መሰረተ ልማት ለማሻሻል “ትምህርት ለትውልድ” በሚል መሪ ቃል የንቅናቄ መድረክ ተካሂዷል።

የዞኑ ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ አሸብር ብረሀኑ እንደገለጹት፤ በዞኑ አጠቃላይ ከሚገኙ 347 ትምህርት ቤቶች ውስጥ አብዛኞቹ የትምህርት ቤቶች ከደረጃ በታች መሆናቸውን ጠቅሰው የትምህርት ቤቶችን መሰረተ ልማት ለማሻሻል ህብረተሰቡ የመማር ማስተማር ሂደቶችን በብቃት እንዲደግፍ ለማስቻልና ትምህርት ቤቶችን በባለቤትነት እንዲይዝ  ለማድረግ ያለመ  ሪፎርም ነው።

በመድረኩ የተገኙት የጎፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዶ/ር ጌትነት በጋሻው ባስተላለፉት መልዕክት በዞኑ  ቁጥራቸው ቀላል የማይባል ትምህርት ቤቶች ንፁህ የመጠጥ ውሃ፣ ተገቢ የመጸዳጃ ቤት አገልግሎት፣ የቤተ ሙከራ እና ሌሎችንም መሰረታዊ መገልገያዎችን እንደማያገኙ ገልጸዋል።

የተጀመረው ንቅናቄ የታለመውን ግብ እንዲመታ  እያንዳዱ ትምህርት ቤት ለልጆች የሚመጥን ውብ፣ ማራኪና ጥራት ያለው ትምህርት መስጠት ብቻ ሳይሆን የተግባር ትምህርት መስጠት የሚያስችሉና ለመማር ማስተማሩ ስራ ምቹ እንዲሆኑ ማድረግ እንዲቻል ከሁሉም ባለ ድርሻ አካላት ሰፊ ስራ ይጠበቃል ብለዋል።

የመድረኩ ተሳታፊዎችም  ትምህርት ስርዓት ውስጥ በርካታ ችግሮች ቢኖሩም ከዋና ዋና ችግሮች መካከል በትምህርት ቤቶች ውስጥ ምቹ የመማሪያ አካባቢ አለመኖሩ መሆኑን አንስተዋል።

የትምህርት ቤቶችን መሰረተ ልማት ለማሻሻል ሁሉም ህብረተሰብ በአቅሙ፣ በጉልበቱ እና እውቅቱ ባለሀብቶች፣ የየትምህርት ቤቶች የቀድሞ ተማሪዎች፣ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች አስፈላጊውን ድጋፍ እንዲያደርጉም ጥሪ አቅርበዋል።

ዘጋቢ፡ አወል ከድር – ከሳውላ ጣቢያችን