በዘንድሮው 2018 ዓ.ም የ6ኛና 8ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ በትኩረት እየተሰራ ነው – የኣሪ ዞን ትምህርት መምሪያ

በዘንድሮው 2018 ዓ.ም የ6ኛና 8ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ በትኩረት እየተሰራ ነው – የኣሪ ዞን ትምህርት መምሪያ

ሀዋሳ፡ ሰኔ 05/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) በኣሪ ዞን በዘንድሮው 2018 ዓ.ም የ6ኛና 8ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ በትኩረት እየሰራ መሆኑን የዞኑ ትምህርት መምሪያ አሰታወቀ።

በኣሪ ዞን የዎባ ኣሪ ወረዳ ትምህርት ጽ/ቤት ተወካይ አቶ እንዳለ ጃመከዜ እንደተናገሩት፤ በወረዳው በሁሉም ትምህርት ቤቶች ለባለድርሻ አካላት ስምሪት በመስጠት እንዲሁም መምህራን ለፈተናው ውጤት መሻሻል አጋዥ የሚሆኑ የፈተና ሞዴሎችን በማሰተማር በኩል ድጋፍ መስጠታቸውን ጨምሮ በርካታ የዝግጅት ምዕራፎች ተጠናቀዋል።

‎የዎባ ኣሪ ወረዳ ትምህርት ጽ/ቤት የትምህርት ምዝናና ፈተና ዳይሬክተር አቶ ማሩ ጀመኖ በበኩላቸው፤ ዘንድሮ 6ኛና 8ኛ ክፍል ተማሪዎች ክልል አቀፍ ፈተና በወረዳው ባሉ ዘጠኝ ክላስተር ጣቢያዎች ላይ እንደሚሰጥና ከዚህ ጋር ተያይዞ የግብዓት አቅርቦትና ለፈተናው ክፍሎችን ምቹ የማድረግ በርካታ ሥራዎች ተከናውነዋል።

‎በዚህም በወረዳው የ6ኛ ክፍል 1193፣ የ8ኛ ክፍል 422 ተማሪዎች የክልል አቀፍ ሚኒስትሪ ፈተና የሚወስዱ መሆናቸውን የገለፁት ዳይሬክተሩ ተማሪዎች ዘንድሮ የተሻለ ውጤት እንዲያስመዘገቡ ሰፊ ጥረት ተደርጓል ብለዋል፡፡

‎በተመሳሳይ የገሊላ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ዩኒቲ መሪ አቶ ማርሸት ክንፉ፤ ለዘንድሮው ክልላዊ የ6ኛ ክፍል ፈተና በከተማ አስተዳደሩ ከ200 በላይ ለሚሆኑ ተማሪዎች ፈተናውን ለመስጠት መዘጋጀቱን ገልጸዋል።

‎ተፈታኝ ተማሪዎችም ፈተናውን ለመፈተን የሚያስችል በቂ ዝግጅት አድርገው በመጠባበቅ ላይ መሆናቸውን አመላክተዋል።

‎የመምሪያው ኃላፊ አቶ እልፍዮስ ባድሜ በዘንድሮ 2018 ዓ.ም ክልል አቀፍ ፈተና እንደ ዞን በ6ኛ ክፍል በ148 ትምህርት ቤቶች አጠቃላይ 8 ሺህ 17 ተማሪዎች ሲፈተኑ በ8ኛ ክፍል 111 ትምህርት ቤቶች 4 ሺህ 477 ተማሪዎች እንደሚፈተኑ ተመላክቷል።

‎በዚህም በዘንድሮ የተሻለ ውጤት እንዲመዘገብ መምሪያው በትኩረት እየሰራ ነው።

‎ዘጋቢ: ፍቃዱ ግዲ – ከጂንካ ጣቢያችን