በክልሉ ለሚገኙ የባህል ፍርድ ቤት ሽማግሌዎች የተዘጋጀ ስልጠና እየተሰጠ ነው

በክልሉ ለሚገኙ የባህል ፍርድ ቤት ሽማግሌዎች የተዘጋጀ ስልጠና እየተሰጠ ነው

የፍትህ ሚኒስቴር ከደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል መንግሥት ፍትህ ቢሮ ጋር በመተባበር በክልሉ ለሚገኙ የባህል ፍርድ ቤት ሽማግሌዎች የተዘጋጀ ስልጠና እየተሰጠ ነው።

ስልጠናውን በንግግር የከፈቱት የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጰያ ህዝቦች ክልል ፍትህ ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ ቤተልሔም ዳንኤል፤ የፍትህ ሚኒስቴር በክልሉ ከ700 በላይ በሚሆኑ ባህላዊ ፍርድ ቤቶች እየሰራ ነው ብለዋል።

በዚህም ከ30 በላይ ለሚሆኑ ባህል ምክር ቤቶች እየሰጠ ላለው ድጋፍም ምስጋና አቅርበዋል።

የኢፌዴሪ ፍትህ ሚኒስቴር ዴኤታ ኤርሚያስ የማነብርሃን (ዶ/ር)፤ ለብዙ ዘመናት በባህላዊ የግጭት አፈታት ውስጥ ባህላዊ ዳኝነት ሚናው የጎላ ነው ብለዋል።

ይህ ባህል ሳይበረዝ መቀጠል እንዳለበት ታስቦና በመንግስት በኩል ለ3 ዓመታት መሠራቱን ጠቁመዋል።

ይህም በ 9 ክልሎች ተግባራዊ እየሆነ መሆኑን የገለጹት ኤርሚያስ የማነብርሃን (ዶ/ር)፤ ከእነዚህም ውስጥ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል አንዱ መሆኑንም አስረድተዋል።

የባህላዊ ፍርድ ቤት ዳኞች የክህሎት ውስንነትን የሚቀርፍ ስልጠና እየተሰጠ መሆኑን ገልጸው፤ የፍትህ ሚኒስትሩ አስፈላጊውን ሁሉ ድጋፍ እያደረገ መሆኑ አስረድተዋል።

መንግሥት የህብረተሰቡን የፍትህ ጥያቄ ለመመለስ በሚያደረገው ጥረት ውስጥ የባህላዊ ዳኝነት ሥርዓት ፋይዳው የጎላ መሆኑንም ገልጸዋል።

ዘጋቢ፡ ሀብታሙ ገብሬ – ከቦንጋ ጣቢያችን