7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በሰላማዊ መንገድ እንዲጠናቀቅ የሁሉም የክልሉ ነዋሪ ሚና ከፍተኛ ነበር – ርዕሰ መስተዳድር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር)

7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በሰላማዊ መንገድ እንዲጠናቀቅ የሁሉም የክልሉ ነዋሪ ሚና ከፍተኛ ነበር – ርዕሰ መስተዳድር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር)

ሀዋሳ፡ ሰኔ 02/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በሰላማዊ መንገድ እንዲጠናቀቅ የሁሉም የክልሉ ነዋሪ ሚና ከፍተኛ እንደነበር የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) ገለፁ፡፡

ከምርጫ ድል ማግስት፣ ጠንካራ መንግስት በሚል መሪ ቃል ክልላዊ የምክክር መድረክ በቦንጋ ከተማ እየተካሄደ ነው።

7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ኢትዮጵያን አሸናፊ ያደረገና ታሪካዊ ጠላቶችን አንገት ያስደፋ ስኬት እንደሆነ የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) ገልፀዋል።

የቅድመ ምርጫና የምርጫ ወቅት በከፍተኛ ስኬት መከናወኑ የክልሉ ህዝብ ለሀገሩና ለፓርቲው ብልፅግና ምን ያኽል አለኝታ እንደነበር ያሳየበት በመሆኑ አመራሩም ይህንን ተገንዝቦ በጥንካሬ ማገልገል እንዳለበትም ርዕሰ መስተዳድሩ አሳስበዋል።

ቅድመ ምርጫ ወቅት አመራሩ ከህዝቡ ጋር በመናበብ ምርጫው ፍፁም ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ እንዲሆን ያበረከቱት አስተዋፅዖም ከፍተኛ እንደነበር ተገልጿል።

የክልሉ ብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ፍቅሬ አማን በበኩላቸው፤ ፓርቲው የቅድመ ምርጫ፣ የምርጫ ወቅትና ድህረ ምርጫ ወቅቶችን በመለየት ግልፅ እቅድ በማስቀመጥ የሚታይ ስኬት ተመዝግቧል ብለዋል።

ሕዝቡ በድምፁ የሰጠውን አደራ በታማኝነት መወጣት እንደሚገባም አቶ ፍቅሬ አስገንዝበዋል።

በመድረኩ በክልሉ ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ነጋ አበራ ሰነድ እየቀረበ ሲሆን፤ በቀጣይ ሥራዎች ዙሪያ ሰፊ ውይይት ይደረጋልም ተብሎ ይጠበቃል።

በመድረኩ የክልል ከፍተኛ አመራሮች፣ የ6 ዞኖች የሥራ አስፈጻሚዎች፣ የየከተማ አስተዳደር ከንቲባዎችና የፓርቲ ጽሕፈት ቤት ኃላፊዎች ተገኝተዋል።

ዘጋቢ፡ ተመስገን አሰፋ – ከቦንጋ ጣቢያችን