2ኛው ዙር ዓለም አቀፍ የምርምር ኮንፍረንስ በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ መካሄድ ጀምሯል

2ኛው ዙር ዓለም አቀፍ የምርምር ኮንፍረንስ በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ መካሄድ ጀምሯል

በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ አዘጋጅነት “በጥንካሬ በመቋቋም ወደ ዘላቂ ዕድገት ለመሻገር የሚረዱ መዋቅራዊ የለውጥ መንገዶች” በሚል መርህ 2ኛው ዓለም አቀፍ የምርምር ኮንፍረንስ እየተካሄደ ይገኛል።

የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት አብዱልሙህሲን ሀሰን (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንደገለፁት፤ ኮንፍረንሱ የማህበረሰቡን ችግሮች በሚፈቱ የምርምር ርዕሶች ላይ በማተኮር ማህበረሰባዊ ለውጥ ማምጣት እንዲቻል ሁሉም የድርሻውን አስተዋጽኦ የሚያበረክትበት ነው።

ስለሆነም የኮንፍረንሱ ተሳታፊዎች በሚቀርቡ የጥናትና ምርምር ስራዎችና ግኝቶቻቸው ላይ ልምድና ተሞክሮ ለመለዋወጥ ዕድል እንደሚፈጥርላቸው በመጠቆም በቆይታቸው ጥያቄ በማንሳት ፣ ምልከታቸውን በመሰንዘር እና ምሁራዊ ትስስራቸውን ይበልጥ በማጠናከር የነቃ ተሳትፎ እንዲያደርጉ አሳስበዋል።

የዩኒቨርሲቲው የምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝዳንት ዮሀንስ ገብሩ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በዩኒቨርስቲው በምርምር እና በቴክኖሎጂ ሽግግር ዘርፍ እየተከናወኑ የሚገኙ ተግባራት ከጊዜ ወደ ጊዜ ውጤታማ እየሆኑ መምጣታቸውን ገልፀዋል።

በኮንፍረንሱ ላይ 19 የምርምር ሥራዎች እንደሚቀርቡም አስታውቀዋል።

በኮንፍረንሱ ላይ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የፖሊሲ ጥናትና ምርምር ተቋም ዋና ዳይሬክተር አክመል መሐመድ (ዶ/ር)፣ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጣሰው ወልደሃና (ፕሮፌሰር) ቁልፍ ንግግር አቅራቢ፣ የወልቂጤ ዩኒቨርስቲ አካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዚዳንት ሀብቴ ዱላ (ዶ/ር) ጨምሮ ሌሎች ጥናት አቅራቢዎች፣ የዩኒቨርሲቲው አመራሮችና መምህራን እንዲሁም ሌሎች እንግዶች እየተሳተፉ ይገኛሉ።

ዘጋቢ፡ ሚፍታ ጀማል – ከወልቂጤ ጣቢያችን