7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በሰላም ለመጠናቀቁ የመላው የክልሉ ህዝብ ተሳትፎ ላቅ ያለ ድርሻ ማበርከቱን የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋር ምክር ቤት ገለፀ

7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በሰላም ለመጠናቀቁ የመላው የክልሉ ህዝብ ተሳትፎ ላቅ ያለ ድርሻ ማበርከቱን የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋር ምክር ቤት ገለፀ

የጋራ ምክር ቤቱ የምርጫውን በሰላም መጠናቀቅ አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል፡፡

የጋራ ምክር ቤቱ ለመገናኛ ብዙሃን በሰጠው መግለጫ ለምርጫው በሰላም መጠናቀቅ የመላው ህዝብ ሚና ከፍተኛ እንደነበር ተጠቅሷል።

በሰላማዊ መንገድ እንዲጠናቀቅ በማድረግ ረገድም የተፎካካሪ ፓርቲዎች ያሳዩት ስነ ምግባርም የሚደነቅ መሆኑን የጋራ ምክር ቤት አስታውቋል።

7ኛው ጠቅላላ ምርጫ እስካሁን ከተደረጉት ምርጫዎች የተሻለ አሳታፊና ተዓማኒ እንደነበር የክልሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ፀሃፊ አቶ ሰለሞን መኮንን ገልፀዋል፡፡

እንደ አቶ ሰለሞን ገለፃ የጋራ ምክር ቤቱ ምርጫው የተሳካ እንዲሆን ሰፊ የቅድመ ምርጫ ስራዎችን ሁሉንም የፖለቲካ ፓርቲዎችን ባሳተፈ መልኩ መስራቱን ተናግረው የተገኘው ውጤትም የዚህ ማሳያ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ምርጫው የመላው ህዝብ ተሳትፎ የሚፈልግ በመሆኑ ህዝቡ ያሳየው ስክነትና ስነግምባር ስልጡንነትን ያሳየ በመሆኑ ምስጋና ይገባዋል ያሉት ደግሞ የጋራ ምክር ቤቱ የስራ አስፈፃሚ አባል ወ/ሪት መቅደስ መኮንን ናቸው፡፡

በምርጫ ወቅት የተስተዋለው እርጋታና ስነ-ስርዓት በድህረ ምርጫ ወቅትም ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትም ጠቅሰዋል፡፡

የጋራ ምክር ቤቱ ምክትል ሰብሳቢ አቶ ግርማ ባሻ በበኩላቸው የዘንድሮው ምርጫ እንደ ክልል በርካታ ተፎካካሪ ፓርቲዎችና ተወዳዳሪ እጩዎች የተሳተፉበት ከመሆኑ በላይ የመራጩ ህዝብ ቁጥርም ከፍተኛ እንደነበር ተናግረዋል፡፡

በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የሚገለጸውን ውጤት በጸጋ ለመቀበል መዘጋጀታቸውንም የምክር ቤቱ ሥራ አስፈፃሚዎች ገልጸዋል።

ዜጎችም ወደ መደበኛ ሥራቸው በመመለስ የዕለት ተዕለት ተግባራቸውንም እንዲያከናውኑ ጥሪ ቀርቧል።

ምክር ቤቱ ለምርጫው ስኬታማነት አስተዋፅዖ ላበረከቱ አካላት  ምስጋና አቅርቧል፡፡
 
ዘጋቢ፡ ተመስገን አሰፋ – ከቦንጋ ማስተባበሪያ