በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በመታገዝ በዝንጅብል ምርት የተሰማሩ አርሶ አደሮች ተጠቃሚ መሆናቸውን ገለፁ

በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በመታገዝ በዝንጅብል ምርት የተሰማሩ አርሶ አደሮች ተጠቃሚ መሆናቸውን ገለፁ

የዝንጅብል ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን በወላይታ ዞን ቦምቤ ከተማ አስተዳደር አስታወቀ፡፡

ካነጋገርናቸዉ አርሶ አደሮች መካከል አርሶ አደር ተፈራ ደለ በበልግ እርሻ ወቅት የመካናይዘሼን እርሻ ዘዴ በመጠቀም ከ6 ሄክታር በላይ ማሳ በዝንጅብል መሸፈኑንና አስፈላጊ ግብዓት መጠቀሙን ተናግረዋል፡፡

አክለውም በማሳቸው ከ20 በላይ ለሥራ አጥ ወጣቶች የስራ ዕድል መፈጠሩን አንስተው ከዝንጅብል ምርት ከሚያገኙ ገቢ ልጆችን ከማስተማር በተጨማሪ በከተማው የመኖሪያ ቤት መስራታቸውን ገልጸዋል፡፡

ዝንጅብል ጠቀሜታ ካላቸው ሰብሎች የተሻለ መሆኑን የጠቀሱት አቶ ተፈራ ዘንድሮ በማሳው ላይ ከተተከለው ከአንድ ሺህ በላይ ኩንታል ምርት እንደሚጠበቅ አንስቷል፡፡

ሌላኛዉ አርሶ አደር ማጋዜ ደለ ከ2 ሄክታር በላይ ማሳ ላይ ዘመናዊ የእርሻ አጠቃቀም በመከተል እየሠራ መሆኑን በመጠቆም ከሃምሳ ኩንታል በላይ  የዝንጅብል ምርት እንደሚጠበቅ ተናግሯል ።

ከዚህ በፊት ባመረቱት የዝንጅብል ምርት የተሻለ ህይውት እየመሩ መሆናቸውን ተናግረዋል ።

አርሶ አደሩ ከፍተኛ ጥራት ያለው ዝንጅብል በስፋት በማምረት የተሻለ ገቢ ለማግኘት እንዲያስችል በግብርና ተቋማት በኩል በቂ ድጋፍ መደረግ እንዳለበት ጠይቀዋል፡፡

በከተማ አስተዳደር የግብርና ጽ/ቤት ኃላፊው አቶ አማሬ አለሙ በበኩላቸው የአከባቢ አየር ሁኔታው ለዝንጅብል ምርትና ምርታማነት ምቹ መሆኑን ጠቅመው በዘንድሮው በበልግ ወቅት ከ 1ሺህ ሃምሳ በላይ ሄክታር ማሳ በዝንጅብል ምርት መሸፈኑን ተናግረዋል፡፡


ምርትና ምርታማነት መጠን ለመጨመር ግብአት ለአርሶ አደሮች በወቅቱ መቅረቡን የተናገሩት ኃላፊው የምርት መጠን እንዳይቀንስ ለማድረግ ፀረ ተባይ ኬሚካሎች ለአርሶ አደሮች ከመስጠት በተጨማሪ ከባንክ ብድር የእርሻ መሳሪያዎች በቀላሉ የሚያገኙበት ሁኔታ እየተመቻቸላቸው መሆኑን ተናግረዋል ።


አዘጋጅ ፡ መሠለ ማርካ – ከዋካ ጣቢያችን