በሸካ ዞን የሚገኙ ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የተሻለ ዴሞክራሲያዊ አሠራር የታየበት ስለመሆኑ ተናገሩ

በሸካ ዞን የሚገኙ ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የተሻለ ዴሞክራሲያዊ አሠራር የታየበት ስለመሆኑ ተናገሩ

በወቅቱ የኢዜማ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተወዳዳሪ ታደለ ቆንጥር ሀገርን መገንባት ከዜሮ በመነሳት ሳይሆን ባለው ላይ መጨመር እንደሆነ ተናግረው ለምርጫው ሰላማዊነትና ፍትሀዊነት ምህዳሩ የሰፋ ፉክክር የታየበት ከመሆኑም በላይ ለዴሞክራሲ መጎልበት ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው ተናግረዋል።

የነጻነት እኩልነት ፖርቲ ሊቀመንበር አቶ ሀይሉ ተስፋዬ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ትችላለች፤ ብዙ ችግሮችን አልፋ የማይቻሉ የሚመስሉ ታላላቅ ሀገራዊ ፕሮጀክቶችን አሳክታ አሳይታለች ብለው በዘንድሮም ምርጫ ከወትሮው በተለየ መልኩ የህዝብ ተሳትፎ የታየበትና ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ ተከናውኗል ብለዋል።

የሸካ ዞን ቴፒ ምርጫ ክልል የሰላም ለኢትዮጵያ ጥምረት ፓርቲ አባልና የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እጩ ተወዳዳሪ አስማማው አለሙ፤ የዘንድሮ ምርጫ ካርድ ተቀብሎ እስከሚመርጥበት የነበረው ሂደት ሥርዓቱን የጠበቀ እንደነበርና ህዝቦች ያለማንም ጣልቃ ገብነት ይበጀኛል ያሉትን የመረጡበት እንደሆነና ውጤቱ ምንም ሆነ ምን የማሸነፍና የመሸነፍ ጉዳይ ብቻ ሳይሆን ሀገርን የማስቀጠል እና ለሀገር ዲሞክራሲ ግንባታ በጋራ መቆም ከሁሉም እንደሚጠበቅ ማሳያ ነው ብለዋል።

የሸካ ዞን ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ አለማየሁ አለሙ፤ ባለፉት ዘመናት ኢትዮጵያ አፍርሶ የመገንባትና እና የአቢዮት ፖለቲካ ውስጥ እንደነበረችና ያም ስርዓት ዕድገቷን ሲያቀጭጭ እንደነበር አስታውሰው ሀገሪቱ በዴሞክራሲያዊ አስተዳደር ስርዓት ውስጥ ገብታ ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ማካሄድ ከጀመረች ዘንድሮ 7ኛዋ እንደሆነ ተናግረዋል።

የዘንድሮ ምርጫ ከእስካሁኑ በተለየ ሁኔታ ከጅምር ሂደት እስከ ድምጽ አሰጣጡ ድረስ በመልካም ስነ-ምግባር የታጀበ ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ እንዳለፈ አንስተዋል።

አቶ አለማየሁ በየደረጃው ለምርጫው መሳካት የበኩላቸውን ለተወጡ አካላት በሙሉ፣ ገዥው ፓርቲ፣ መንግስት፣ የሚዲያ አካላት፣ ገለልተኛ አካላት፣ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን፣ የፀጥታ አካላትና መላው ህዝቡን አመስግነዋል።

ዘጋቢ: ምንታምር አስፋው