በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል 7ኛዉ ጠቅላላ ምርጫ በሰላም መጠናቀቁን የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ

በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል 7ኛዉ ጠቅላላ ምርጫ በሰላም መጠናቀቁን የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ

‎የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ሽመልስ ካሳ የምርጫ ወቅት የፀጥታ ስራን አስመልክቶ መግለጫ ሰጥተዋል።

ኮሚሽነሩ በሰጡት መግለጫ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የፀጥታ ተቋም ከምርጫ ሂደቱ ቀደም ብሎ በክልሉ ከዞን ጀምሮ እስከታች ድረስ የፀጥታ ግብረ ሀይል አቋቁሞ በጋራ ሲሰራ እንደነበር ገልፀዋል።

ማህበረሰቡም ወንጀል ነክ ከሆኑ ጉዳዮች እራሱን እንዲያገልና ከፀጥታ ሀይል ጋር በመተባበር ወንጀልን የመከላከል ተግባር ላይ ትኩረቱን እንዲያደርግ በተለያዩ መንገዶች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎች ሲሰሩ መቆየታቸውን ተናግረዋል።

ቀደም ሲሉ በነበሩ ሂደቶችም የፀጥታ ግብረ ሀይሉ የስራ ውጤት በየጊዜው በርዕሰ መስተዳድሩ ይገመገማል ያሉት ኮሚሽነሩ፤ ይህ ተግባር ክልላችን ከምርጫው ሂደት ቀደም ብሎ ለሰላም እና ፀጥታ መስፈን የሚሰጠውን ትኩረት ያሳያል ብለዋል።

7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በሰላም እንዲጠናቀቅ ከምርጫ በፊት ተጨማሪ የፀጥታ ሀይልን የማደራጀት ስራ መሰራቱንም ገልፀዋል።

በቅድመ ዝግጅቱ በምርጫ እለት የምርጫውን ሂደት ሊያስተጓጉሉ ይችላሉ ተብለው በታሰቡ ጉዳዮች ላይ ከሁሉም ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመወያየት ቅድመ ጥንቃቄ የማድረግ ስራ መሰራቱንም አብራርተዋል።

ምርጫው በሰላም እንዲጠናቀቅ በዋናነት የክልላችን ማህበረሰብ ትልቁን ሚና ተወጥቷል ያሉት ኮሚሽነሩ፤ ለስራው መሳካት ከፀጥታ ሀይል ጎን ለቆሙ አጠቃላይ የማህበረሰብ ክፍሎች ምስጋና አቅርበዋል።

‎ማህበረሰቡ በድህረ ምርጫ ወቅት ከሚሰራጩ ሀሰተኛ መረጃዎች እራሱን እንዲጠብቅና ለአካባቢያዊ ሰላም ከፀጥታ አካላት አጋር በጋራ የመስራት ልምዱን እንዲያጠናክር መልዕክት አስተላልፈዋል።

‎ ዘጋቢ፡ ሸዊት ሂርጶ