መብታችንን ተጠቅመን ድምጻችንን ለመስጠት ተዘጋጅተናል – በሸካ ዞን የአንድራቻ ወረዳ ነዋሪዎች

መብታችንን ተጠቅመን ድምጻችንን ለመስጠት ተዘጋጅተናል – በሸካ ዞን የአንድራቻ ወረዳ ነዋሪዎች

‎የምርጫ ካርዳቸውን ተጠቅመው ድምጽ ለመስጠት ነገን እየጠበቁ መሆኑን በሸካ ዞን የአንድራቻ ወረዳ ነዋሪዎች ገልጸዋል።

‎7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ሰላማዊ፣ ፍትሐዊ እና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ የድርሻቸውን ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውን ነዋሪዎቹ ተናግረዋል።

‎በአንድራቻ ወረዳ ጌጫ ከተማ ነዋሪነታቸውን ካደረጉ አስተያየት ሰጪዎች መካከል አቶ መልካሙ አንደሞ እና አንድነት ሸሎ፤ የምርጫ ካርዳቸውን አስቀድመው ማውጣታቸውን እና ነገ ግንቦት 24ን በጉጉት በመጠባበቅ ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል።

‎ለሀገር እድገት ይጠቀማል የሚሉትን ፓርቲ በመምረጥ መብታቸውን ለመጠቀም የምርጫውን ቀን በመጠባበቅ ላይ መኾናቸውን አንስተዋል።

‎ዜጎች የምርጫ ካርዳቸውን መጠቀም አለባቸው ያሉት ደግሞ የሼራ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት ወ/ሮ ፍሬህይወት ካሮ እና የገቲባ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ከበደ ደስታ እንዲሁም ወጣት አሳምነው ታዬ ናቸው።

‎ከሁሉም ነገር ለሀገር ሠላም ቅድሚያ መስጠት ይገባል ያሉት ነዋሪዎቹ፤ ምርጫው በሰላም እንዲጠናቀቅ የበኩላቸውን እንደሚወጡም ተናግረዋል።

‎ምርጫው ፍትሐዊ እና ዴሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ እንዲጠናቀቅ ሁሉም የበኩሉን ሊወጣ እንደሚገባም መልዕክት አስተላልፈዋል።

‎ዘጋቢ: ታሪኩ ታደሰ – ከማሻ ጣቢያችን