የሕዝባችንን የልማት ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ የመመለስና ሜጋ ፕሮጀክቶችን በፍጥነት የማጠናቀቅ ቁርጠኝነታችንን አጠናክረን እንቀጥላለን-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
ሀዋሳ፡ ሐምሌ 05/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) ፈተናዎችን ወደ ዕድል በመቀየር የሕዝባችንን የልማት ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ ለመመለስና ሜጋ ፕሮጀክቶችን በፍጥነትና በጥራት ጀምሮ የማጠናቀቅ ቁርጠኝነታችንን አጠናክረን እንቀጥላለን ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የደብረ ማርቆስና የአካባቢው ሕዝብ ለዓመታት በጉጉት ሲጠብቀው የነበረውን፣ ለ30 ዓመታት ያህል ተቋርጦ የቆየውንና በአዲስ መልክ ተሻሽሎ ደረጃው ከፍ ብሎ የተገነባውን የደብረ ማርቆስ ንጉሥ ተክለ ሃይማኖት አውሮፕላን ማረፊያ ዛሬ በይፋ መርቀዋል።
በ2 ሺህ 400 ሜትር ርዝመትና በ30 ሜትር ስፋት የተገነባው አውሮፕላን ማረፊያው፣ እንደ Q400 እና ቦይንግ 737 ያሉ ግዙፍ የሕዝብና የጭነት አውሮፕላኖችን ማስተናገድ የሚያስችል አቅም አለው።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ እንደገለጹት፤ የአውሮፕላን ማረፊያው ተመርቆ ሥራ መጀመሩ የደብረ ማርቆስ ከተማ ነዋሪዎችን የዘመናት ጥያቄ የመለሰ ነው።
የአየር ማረፊያው ለአገልግሎት መብቃትም የአካባቢውን የንግድ፣ የኢንቨስትመንትና የቱሪዝም እንቅስቃሴ በከፍተኛ ሁኔታ በማነቃቃት፣ ለሀገራችን የኢኮኖሚ ዕድገት አዲስ ምዕራፍ እንደሚከፍት አስገንዝበዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ የደብረ ማርቆስ ከተማን ታሪካዊ አመጣጥና ቀድሞ የነበራትን የልማትና የስልጣኔ ገናናነት አስታውሰዋል።
መደመር ወደኋላ መለስ ሲል መልካሙን የሚያወሳና የሚያስታውስ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የቀድሞና የአሁን አመራሮችን ጥረትና አስተዋጽኦ በቅጡ ማስታወስ እንደሚገባ ገልጸዋል።
ከተማዋ በ1951 ዓ.ም በሀገሪቱ ከነበሩ 20 ከተሞች ተወዳድራ አንደኛ መውጣቷን ያወሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ አሁን ላይ ያንን የቀድሞ ክብሯን ለማግኘት የሚያስችል ቁመና ላይ መሆኗን ማረጋገጥ የእያንዳንዱ ከተማዋን የሚወድ ዜጋ ኃላፊነት መሆን እንዳለበት አስገንዝበዋል።
የአውሮፕላን ትራንስፖርት መጀመሩ እንዳለ ሆኖ በየብስ ትራንስፖርት የመንቀሳቀስ ጉዳይም በጋራ ጥረት ወደ ተሟላ ሁኔታ መመለስ እንዳለበት ገልጸዋል።
በአሁኑ ወቅት የዘር፣ የመከፋፈል፣ የጎጠኝነትና የጽንፈኝነት እሳቤዎችን መጸየፍ እንደሚያስፈልግ አስታውሰዋል።
ትናንት ጎጃምንና ወለጋን ያስተሳሰረች፣ የተጋመደ ማኅበራዊ ቁርኝት የነበረባት ደብረ ማርቆስ ለሌላው አርአያና የአንድነት ምልክት መሆን እንደሚገባት አጽንኦት ሰጥተዋል።
በዓባይ ሸለቆና በማዶው አካባቢ ወደ አዲስ አበባ ለመሻገር እንቅፋት የሆኑ ሽፍቶችን በጋራ ታግሎ ማስወገድ ሲገባ፣ ተጨማሪ ሽፍቶችን ማበራከት ተገቢ አይደለም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ መከፋፈልም ለማንም እንደማይጠቅም ጠቁመዋል።
የሚሻለውም የሚያለያዩ ጥቃቅን ነገሮችን ትቶ በጋራ መሻት በሆኑት በሰላምና በልማት ጉዳዮች ላይ መሥራት እንደሆነ አስረድተዋል።
የአየር ትራንስፖርት መጀመሩ በቀን ሦስት ጊዜ በረራ በማድረግ ምቾት የሚፈጥር ቢሆንም፣ የየብስ ትራንስፖርትን መጠቀም ለሚፈልጉ ዜጎች ሰላም በእጅጉ አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል።
መንግሥት ለውይይትና ለንግግር ለሚፈልግ ለማንኛውም አካል በሩ ክፍት መሆኑን በመግለጽ፤ የማያስማሙ ጉዳዮች ካሉ በሰላማዊና በሰለጠነ የፖለቲካ አግባብ መፍታት እንደሚቻል ጥሪ አቅርበዋል።
ልማት በባህሪው ጊዜን፣ ትብብርንና ጥበቃን እንደሚፈልግ ያስረዱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ የጎደለውን ልማት፣ ብልፅግና፣መተማመንና መከባበር ለመሙላትና ለልጆቻችን የተሻለች ሀገር ለማስረከብ በጋራ መትጋት እንደሚገባ አሳስበዋል።
በመጨረሻም ለቀጣዩ ትውልድ አረንጓዴ አሻራ በማሳረፍ አንድነት እንዲያብብ ማድረግና የነገዋን ኢትዮጵያ ለልጆች ምቹ ለማድረግ ሁሉም በአንድነት እንዲረባረብ ጥሪ አቅርበዋል።

More Stories
ሞዴል የቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችን መሠረተ ልማት ማሟላትና ምቹ የመማሪያ ከባቢን ለልጆች መፍጠር ለቀጣዩ የትምህርት ደረጃዎች መሠረት መሆኑ ተገለጸ
በጎፋ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የህግ የበላይነትን ለማረጋገጥና ጥራትና ተዓማኒነት ያለው የፍትህ አገልግሎት በመስጠት ረገድ ውጤታማ ተግባራት መከናወናቸውን የዞኑ ፍትህ መምሪያ አስታወቀ
ለህብረተሰቡ ፈጣን እና ቀልጣፋ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን የሀላባ ቁሊቶ ከተማ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት አስታወቀ