‎በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ድምጽ ለመስጠት መዘጋጀታቸውን የዲላ ከተማ ነዋሪዎች ተናገሩ

‎በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ድምጽ ለመስጠት መዘጋጀታቸውን የዲላ ከተማ ነዋሪዎች ተናገሩ

‎ህብረተሰቡ በሰላማዊ መንገድ ድምጹን በመስጠት ንቁ ተሳትፎ ማድረግ እንዳለበትም ተጠይቋል።

‎አገልጋይ ዘውዴ ከበደ የዲላ ከተማ ነዋሪ ናቸው። ሀገር ሰላም ሆኖ ሰላማዊ ምርጫ እንዲካሄድ በጸሎት እየተጉ ድምጻቸውን ለመስጠትም ቀኑን እየጠበቁ እንዳለ ተናግረዋል።

‎የሰው ልጅ ዘርቶ ማፍራት፣ ሠርቶ መብላትና ወጥቶ መግባት የሚችለው ሰላም ሲኖር ብቻ በመሆኑ ሁሉም ለሰላም የበኩሉን አስተዋጽኦ ሊያበረክት ይገባል ብለዋል።

‎በዲላ ከተማ በወንዶች የውበት ሳሎንና በልብስ ስፌት ሥራ ላይ የተሰማሩት ወጣት ቢኒያም ጴጥሮስና አቶ ቸርነት አለሙ፤ ይበጀኛል ይሆነናል የሚሉትን ለመምረጥ መዘጋጀታቸውን በመግለጽ ሁሉም ዜጋ ምርጫው በሰላማዊ መንገድ እንዲጠናቀቅ የበኩሉን እንዲወጣም ጠይቀዋል።

‎ምርጫ የአንድ ሀገር ዴሞክራሲ መገለጫ ነው ያለችው ደግሞ ወይዘሪት ስምረት ኢያሱ፤ ወጣቶች ለሀገራቸው የነገ መጻኢ ተስፋ በሰላማዊ መንገድ ድምጻቸውን ሊሰጡ ይገባል ብለዋል።

‎ዕለተ ሰኞ ማለዳን ከነቤተሰቦቻቸው ድምጽ ለመስጠት በጉጉት እየተጠባበቁ እንዳለ የገለጹት ሌላኛው አስተያየት ሰጪ አርሶአደር ታምሩ ጎበና፤ ህብረተሰቡ ዴሞክራሲያዊ መብቱን ተጠቅሞ ድምጽ ሊሰጥ እንደሚገባ አሳስበዋል።


‎ዘጋቢ: ውብሸት ካሳሁን – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን