በሀዲያ ዞን ሶሮ 02 ምርጫ ክልል ቁሳቁስ ወደ ምርጫ ጣቢያ እየተሰራጨ ይገኛል

በሀዲያ ዞን ሶሮ 02 ምርጫ ክልል ቁሳቁስ ወደ ምርጫ ጣቢያ እየተሰራጨ ይገኛል

‎ከነገ በስቲያ ለሚከናወነው 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በሶሮ 02 ምርጫ ክልል ለሚገኙ የምርጫ ጣቢያዎች የምርጫ ቁሳቁስ እየተሰራጨ ይገኛል፡፡

‎በሀዲያ ዞን ካሉ ምርጫ ክልሎች አንዱ የሆነው በሶሮ 02 ምርጫ ክልል ለሚገኙ ለሁሉም ምርጫ ጣቢያዎች የምርጫ ቁሳቁስ ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን የደቡብ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት በስፍራው ተገኝቶ መመልከት ችሏል።

‎በምርጫ ክልሉ 97 ምርጫ ጣቢያዎች ያሉ ሲሆን እስካሁን ለ50 ምርጫ ጣቢያዎች የምርጫ ቁሳቁስ መሰራጨቱን የሶሮ 02 ምርጫ ክልል አስተባባሪ ሰላሙ ታረቀኝ ተናግረዋል።

‎ለቀሩት ምርጫ ጣቢያዎች ዛሬ እና ነገን ጨምሮ ሙሉ ለሙሉ ተሰራጭቶ ይጠናቀቃል ያሉት አስተባባሪዉ፤ ዝግጅቱ በጥሩ ሁኔታ ላይ እንዳለ ጠቁመዋል።

‎የምርጫ አስተባባሪዎችም ቁሳቁሶቹ በተገቢው እንዲደርሱ እያደረጉ መሆናቸውን አክለዋል።

‎የጃጁራ ከተማ አስተዳደር ፖሊስ አዛዥ ረ/ኢንስፔክተር ብርሃኑ ደቦጭ በበኩላቸው እንዳሉት፤ ኦረንቴሽን ከመስጠት ጀምሮ ከፀጥታና ደህንነት ጉዳዮች ጋር ተያይዞ ካለምንም ችግር ሰላማዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ሁሉም የፀጥታ አካላት ተሰማርተዋል።

‎ እስከአሁን ባለዉ በጣቢያዎቹ ምንም ስጋት እንደሌለና እስኪጠናቀቅ ድረስም ከመራጩ ህብረተሰብና ምርጫ ጣቢያዎች ጋር በትብብር እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል።

‎በምርጫ ክልሉ ያሉ አብዛኛዎቹ የምርጫ ጣቢያዎች ዝግጅታቸውን እየጨረሱ መሆናቸውም ተመላክቷል።
ዘጋቢ፡ ብዙነሽ ዘዉዱ