የ41 ዓመቱ ኮከብ ክሪስቲያኖ ሮናልዶ ዶስ ሳንቶስ አቬይሮ ስሙ በፖርቱጋል ብሔራዊ ቡድን ስብስብ ውስጥ መካተቱ ተረጋግጧል።
ይህ በስፖርቱ ታሪክ ታይቶም ተሰምቶም የማይታወቅ አዲስ ታሪካዊ ምዕራፍ ነው።
ዘንድሮው አሜሪካ፣ ካናዳ እና ሜክሲኮ በጣምራ በሚያዘጋጁት ዓለም ዋንጫ ላይ ኮከቡ ለአንድ ሰከንድ እንኳ ወደ ሜዳ ከገባ፣ በዓለም የእግር ኳስ ታሪክ 6 የተለያዩ የዓለም ዋንጫዎች ላይ የተጫወተ የመጀመሪያው ብቸኛ ተጫዋች በመሆን ስሙን በወርቅ ቀለም ያፅፋል።
እ.ኤ.አ በ2006 በጀርመን ምድር የዓለም ዋንጫ የመጀመሪያ ተሳትፎውን ያደረገው ወጣቱ ሮናልዶ፣ ከ20 ዓመታት በኋላ ዛሬም በዕድሜ ሳይገደብ በንጉሣዊ ግርማው ይመራል።
በአምስት ተከታታይ የዓለም ዋንጫዎች ላይ ግብ ያስቆጠረ የመጀመሪያው ሰው ሲሆን፣ ዘንድሮም ያንን ክብረ ወሰን የማራዘም ዕድል አለው።
አምስት ጊዜ የባሎንዶር ሽልማትን ያነሳው ሮናልዶ፣ ለሀገሩ ፖርቱጋል የመጀመሪያውን የዓለም ዋንጫ ስኬት ለመስጠት አሁንም በአዳኝነቱ ቀጥሏል።
የፖርቱጋል ከፍተኛው ጉዞ በ2006 ሮናልዶ ገና ብቅ ሲል ያሳካችው የግማሽ ፍጻሜ ደረጃ ነበር።
ፖርቱጋል 4 ግብ ጠባቂዎችን ያካተተ የ27 ተጫዋቾች ስም ዝርዝር ይፋ አድርጋለች። ይሁን እንጂ እንደ ፊፋ (FIFA) መመሪያ ማንኛውም ሀገር ይፋዊ የዓለም ዋንጫ ስብስቡን ከ23 እስከ 26 ተጫዋቾች መካከል ብቻ ማድረግ ስለሚገባው፣ አሰልጣኝ ሮቤርቶ ማርቲኔዝ ስብሰባቸውን ይዘው ወደ ውድድር ስፍራው ከማምራታቸው በፊት አንድ ተጫዋች የመቀነሳቸው ጉዳይ የማይቀር ነው።
አሰልጣኙ 27ኛውን ተጫዋች ያካተቱት በቅርቡ ከዚህ ዓለም በሞት ለተለየው ዲዮጎ ዦታ ክብር ሲሉ እንደሆነም ይነገራል።
ፖርቹጋል በ2026ቱ የዓለም ዋንጫ በምድብ 11 ከዲሞክራቲክ ኮንጎ፣ ኮሎምቢያ እና ኡዝቤክስታን ጋር ተደልድላለች።
ዕድሜ ቁጥር ብቻ መሆኑን በተግባር ያሳየን ይህ እቅጩ የኳስ ጥበበኛ፣ ዘንድሮ የመጨረሻውን የክብር ዘውድ ይደፋ ይሆን?
ዘጋቢ፡ ሙሉቀን ባሳ

More Stories
ወሰን ተሻጋሪ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የእርስ በርስ ግንኙነትና አንድነትን የሚያጠናክር ተግባር መሆኑ ተገለጸ
በክልሉ የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠል አለባቸዉ – ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጥላሁን ከበደ
የሕዝባችንን የልማት ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ የመመለስና ሜጋ ፕሮጀክቶችን በፍጥነት የማጠናቀቅ ቁርጠኝነታችንን አጠናክረን እንቀጥላለን-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)