ለሁለት ቀናት ሲካሄድ የነበረው የቦንጋ ዩኒቨርሲቲ ዓለም አቀፍ የቡና ኮንፈረንስ ተጠናቋል
በቡና ላይ ከፍተኛ ጥናትና ምርምር ያደረጉ አለም አቀፍ የቡና ሳይንስ ተመራማሪዎች ጥናታዊ ጽሑፋቸውን አቅርበዋል።
ጥናታዊ ጽሑፉን ተከትሎ የቡና ልማትንና የግብይት ሥርዓትን በማሳለጥ የአምራቹን ህብረተሰብ ሕይወት ለመለወጥ በሚያስችሉ ተግባራት መሰራት እንዳለባቸው የኮንፈረሱ ተሳታፊዎች ተናግረዋል።
በተመራማሪዎችና በአምባሳደሮቹ የወሺ ግሪን ኮፊ ቡና ልማት ጉብኝት የተደረገ ሲሆን ጎብኝዎቹም ባዩት የቡና ልማት እንክብካቤና የተፈጥሮ ሐብት ጥበቃ ሥራዎች መደሰታቸውን አስረድተዋል።
በቦንጋ ዩኒቨርሲቲ ክትትልና ድጋፍ እየተደረገ የሚገኘው የቦንጋ ብሔራዊ የቡና ሙዚየም ጉብኝት ተደርጓል።
በዩኒቨርሲቲው ግቢ ውስጥ የሚገኘዉ አለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የቡና ላብራቶሪ ጉብኝት ሲደረግ አጠቃላይ የላብራቶሪ አገልግሎት አሰጣጡን በተመለከተ የቡና ሳይንስ ተመራማሪው ዶ/ር ክፍሌ በላቸው ገለጻ አድርገዋል።
የዩኒቨርሲቲው የቦርድ ምክትል ሰብሳቢ ፕሮፌሰር ክፍሌ ወ/ሚካኤል፣ የቦርዱ አባል ዶ/ር ተክለአብ ቡሎና የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝደንት ዶ/ር ደጌላ ኤርጌኖ የማጠቃለያ መድረኩን የመሩ ሲሆን፤ ከቀረበው ምርምር ግኝትም ሆነ ከተሳታፊዎች አስተያየት ለቀጣይ ሥራዎች አጋዥ የሚሆኑ ግብዓቶች እና ከሀገር ውስጥም ሆነ ከውጭ ሀገራት ጋር ቅንጅታዊ አሰራሮችን የሚያጠናክሩ ጉዳዮች መገኘታቸውን ተናግረዋል።
የጥናትና ምርምር ሥራዎቻቸውን ላቀረቡት ተመራማሪዎችና አስተባባሪዎች የምስጋናና የዕውቅና ምስክር ወረቀት ተበርክቶላቸዋል።
የቦንጋ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝደንት ዶ/ር ደጌላ ኤርገኖ አያይዘውም፤ የዓለም ዓቀፍ የቡና ጥናትና ምርምር ኮንፈረንስ መደረጉ አበርክቶው የላቀ መሆኑን ገልጸው ኬት ኮፊ/KET COFFEE/ ከተባለ ዓለም አቀፍ ካምፓኒ ጋር የውል ስምምነት ተፈራርመዋል።
በቦንጋ አለም አቀፍ የቡና ኮንፈረስ ላይ ከፍተኛ ጥናትና ምርምር ያደረጉ አለም አቀፍ የቡና ሳይንስ ተመራማሪዎች፣ አምባሳደሮች፣ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ የካፋ ንጉስና ምክረቾ አባላት ተሳታፊ ሆነዋል።
ዘጋቢ፡ መለሠ ገብሬ – ከቦንጋ ጣቢያችን

More Stories
ባህላዊ እሴትና የወንድማማችነት ትስስርን የሚያድስ የ“ኦዴ ኦሶ” ቤተሰብ ምረቃ ስነ-ስርዓት በልዩ ድምቀት ተካሄደ
የጎፋ ዞን ልማት ማህበር ሥራ አመራር ቦርድ የ3ኛ ሩብ ዓመት የሥራ አፈፃፀም ግምገማ መድረክ አካሄደ
የሀይማኖት ተቋማት በመተባበር እና በመነጋገር ለሀገር ግንባታ በጋራ ልንሰራ ይገባል – የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ሼህ ሀጂ ኢብራሂም ቱፋ