ባህላዊ እሴትና የወንድማማችነት ትስስርን የሚያድስ የ“ኦዴ ኦሶ” ቤተሰብ ምረቃ ስነ-ስርዓት በልዩ ድምቀት ተካሄደ

ባህላዊ እሴትና የወንድማማችነት ትስስርን የሚያድስ የ“ኦዴ ኦሶ” ቤተሰብ ምረቃ ስነ-ስርዓት በልዩ ድምቀት ተካሄደ

ሀዋሳ፡ ሚያዚያ 25/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) በሀድያ ዞን ሻሾጎ ወረዳ በሞሎሊቾ ቀበሌ የቆየውን ባህላዊ እሴትና የወንድማማችነት ትስስርን የሚያድስ የ“ኦዴ ኦሶ” ቤተሰብ ምረቃ ስነ-ስርዓት በልዩ ድምቀት ተካሂዷል።

የባህላዊ ምረቃ ስነ-ስርዓት የሀዲያና የአካባቢውን ማህበረሰብ አንድነት ይበልጥ የሚያጠናክር መሆኑን የሻሾጎ ወረዳ አስተዳደር አስታውቋል።

በዕለቱ የክብር እንግዳ የሀዲያ፣ የከንባታ፣ የስልጤ እና የሀለባ ሀገር ሽማግሌዎች በበዓሉ ላይ በጋራ በመገኘት ለፕሮግራሙ ልዩ ድምቀት ሰጥተውታል።

የየብሄረሰቦቹ የሀገር ሽማግሌዎች እንደየባህላቸው ተራ በተራ በመቆም፣ ለተመራቂው ቤተሰብና ለአካባቢው ማህበረሰብ ሰላም፣ ፍቅርና አንድነትን የሚያውጁ ምርቃቶችን አስተላልፈዋል።

አባቶች በምርቃታቸው ወቅት እንደገለጹት እንዲህ ያሉ መድረኮች በህዝቦች መካከል ያለውን ማህበራዊ መስተጋብር ከማጠናከራቸው ባለፈ፥ ታላላቅ ባህላዊ እሴቶች ሳይበረዙ ለቀጣዩ ትውልድ እንዲተላለፍ ትልቅ ሚና ይጫወታል ብለዋል።

አጠቃላይ የሻሾጎ ዳኛ አድላ ሀብታሙ ዮሐንስ የፕሮግራሙ ዓላማ ምድርቱን ለመባረክ፣ የተማሩና ለሀገር የሚጠቅሙ ዜጎች እንዲወጡ ለትውልድ በረከትን እንደገና ለማስተላለፍ መሆኑን ገልጸዋል።

በምረቃው ስነ-ስርዓት ላይ የሻሾጎ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ግርማ ሎቤ እንደገለጹት የዚህ ዓይነት ባህላዊ እሴቶች ለአካባቢው የሰላም እሴት ግንባታና ለጋራ ልማት ያለው ፋይዳ የጎላ መሆኑን ገልጸዋል ።

የባህላዊ ምረቃ ስነ-ስርዓት የሀድያና የአካባቢውን ማህበረሰብ አንድነት ይበልጥ የሚያጠናክር እንደሆነም አመላክተዋል።

የወረዳ ባህልና ቱርዝም ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ታጁራ ሎላሶ በበኩላቸው የሀድያን አንድነት የሚያጠናክሩ ባሕላዊ እሴቶችን ተጠብቆ ለትውልድ እንዲተላለፉ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።

በመርሃ-ግብሩ በሀድያ ባህላዊ ዜማዎችና በደማቅ የምርቃት ስነ-ስርዓት የታጀበ ሲሆን በታዳሚው ዘንድ ትልቅ መነሳሳትንና የደስታ ስሜትን በመፍጠር በሰላም ተጠናቋል።

ዘጋቢ: ታምራት አለሙ – ከሆሳዕና ጣቢያችን