የምሁራን አንድነትን ማጠናከርና የእርስ በእርስ መከባበር ባህልን ማጎልበት ለአካባቢው ዘላቂ ሠላም መስፈን ወሳኝነት እንዳለው ተመላከተ

የምሁራን አንድነትን ማጠናከርና የእርስ በእርስ መከባበር ባህልን ማጎልበት ለአካባቢው ዘላቂ ሠላም መስፈን ወሳኝነት እንዳለው ተመላከተ

ይህ የተገለጸው በእርስ በርስ መከባበርና የአብሮነት እሴቶች ላይ ያተኮረ የማህበረሰብ ውይይት በደቡብ ኦሞ ዞን ሐመር ወረዳ ኤርቦሬ ከተማ በተካሄደበት ወቅት ነው።

ውይይቱን በጋራ የመሩት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ፣ የመካነ ኢየሱስ እና ብርሃን ወንጌል ቤተ ክርስቲያን የሃይማኖት አባቶች ናቸው።

እርስ በርስ ከመገፋፋት ይልቅ የመደጋገፍ፣ የመከባበርና መፈቃቀር ባህልን ለማሳደግ እግዚአብሔርን መፍራት እና ለእርሱም መገዛት ተገቢ መሆኑን ጠቅሰው፤ በሰላማዊ አስተሳሰብ 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በስኬት እንዲጠናቀቅ ሁሉም የድርሻውን እንዲወጣ አሳስበዋል።

የውይይቱ ተሳታፊዎች በበኩላቸው፤ የምሁራን አንድነትና መደማመጥ ለሀገር ሠላምና ልማት ቁልፍ ድርሻ እንዳለው ተናግረዋል።

የሐመር ወረዳ ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊ እና የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ባርጆሌ ጊኖ፤ የአካባቢውን ልማት ለማፋጠን ምሁራን ተገቢውን ሚና መወጣት አለባቸው ብለዋል።

የሃይማኖት አባቶችም የተሻለ ትውልድ ለመፍጠር፣ ጥላቻን ማስወገድና እርስ በእርስ መከባበርን ለማጎልበት በማለም ላዘጋጁት መድረክ መምስጋናቸውን አቅርበዋል።

ለሀገር ሰላምና እድገት የሁላችንም ጥንካሬ ወሳኝ መሆኑን በማንሳት የብልጽግናን ተልዕኮ ለማሳካት የምሁራን ድርሻ ጉልህ ሊሆን ይገባል ሲሉም ነው ያሳሰቡት።

የዞኑ ሠላምና ፀጥታ መምሪያ ኃላፊ አቶ አብዱባ ሁና፤ ሰላምን ለማጽናትና ብልጽግናን ለማረጋገጥ በመደጋገፍ እና በመከባበር መትጋት ወሳኝነት አለው ብለዋል።

መድረኩ በዚህ ረገድ ገንቢ ሚና የሚጫወት መሆኑን ጠቅሰው፤ 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በስኬት እንዲጠናቀቅ በቅንጅት እየተሠራ እንዳለም ተናግረዋል።

ዘጋቢ፡ አርሻል አራቦ – ከጂንካ ጣቢያችን