በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አንዳንድ አካባቢዎች በተደረገ ድንገተኛ ፍተሻ 25 ሺህ 338 ሊትር ቤንዝልና 62 ሺ 686 ሊትር ናፍጣ በቁጥጥር ስር መዋሉን የክልሉ ንግድና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ አስታወቀ

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አንዳንድ አካባቢዎች በተደረገ ድንገተኛ ፍተሻ 25 ሺህ 338 ሊትር ቤንዝልና 62 ሺ 686 ሊትር ናፍጣ በቁጥጥር ስር መዋሉን የክልሉ ንግድና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ አስታወቀ

‎ከነዳጅ እጥረት ጋር ተያይዞ የሚስተዋለውን ህገ-ወጥ የግብይት ስርዓት ለመቆጣጠር ጠንካራ ስራ እየተሰራ መሆኑንም ቢሮው አረጋግጧል፡፡

‎ቢሮው ከነዳጅ እጥረት እና ከህገ-ወጥ የግብይት ስርዓት ጋር ተያይዞ ለጋዜጠኞች መግለጫ ሰጥቷል።

‎የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ንግድና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ ሰናይት ሰለሞን በመግለጫቸው እንዳሉት፤ የነዳጅ ስርጭትና ግብይት ስርአትን ለመቆጣጠር እንዲያችል ጠንካራ ግብረ ሀይል ተቋቁሞ በክልሉ በ12 ዞኖችና በ 3ቱ ሪጂዮ ፖሊ ከተሞች እየተሠራ ይገኛል።

‎ከዚህ አኳያ ፖሊስን ጨምሮ ከግብረ ሀይሉ ጋር በመሆን እስከታችኛው መዋቅር በተደረገው የቁጥጥር ስርዓትና ድንገተኛ ፍተሻ 25 ሺህ 338 ሊትር ቤንዝልና 62 ሺ 686 ሊትር ናፍጣ በቁጥጥር ስር መዋሉን ገልጸዋል።

‎በዚህ ህገ-ወጥ የግብይት ስርአት ውስጥ የተሳተፉ አራት የንግድ ባለሙያዎች በህግ እየተጠየቁ ሲሆን ነዳጅ የሚያመላልሱና የሚያጓጉዙ 27 አካላትና 8 የማደያ ባለቤቶች በቁጥጥር ስር ውለው በህግ እየተጣራ መሆኑን ወ/ሮ ሰናይት አብራርተዋል።

‎በዚህ መነሻ ህገ-ወጥ የነዳጅ ግብይት ውስጥ የገቡ ስምንት ማደያዎች መታሸጋቸውንም ጠቅሰዋል።

‎ህገ-ወጥ የነዳጅ ግብይት ስርዓቱን ለመቆጣጠር እንዲያስችል በአብዛኛው ማደያዎች የ CCtv ካሜራ እንዲያስገጥሙ የተሰራ መሆኑን አብራርተው፤ የተወሰኑ ማደያዎች ያላስገጠሙ መሆናቸውንም ገልጸዋል።

‎በክልሉ የሚገኙ 113 ማደያዎች በፍትሀዊ መንገድ ለተጠቃሚው ነዳጅ እንዲያደርሱ ጠንካራ ስራ እየተሰራ መሆኑን በመግለጫቸው አንስተዋል የቢሮው ኃላፊ።

‎ህገ-ወጥነቱን በመቆጣጠር ሂደት አጋዥ በመሆን ለሚመለከተው አካል ጥቆማ የሰጡ አካላት ሊመሰገኑ እንደሚገባና ይህ ተግባር ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት በመግለጫቸው አሳስበዋል።

‎ከነዳጅ አኳያ እንደ ሀገር የተቀመጠው አግባብ እንዲተገበር ሁሉም መረባረብ እንዳለበት አሳስበው፤ ለተግባራዊነቱም እንደ ቢሮ ጠንካራ ክትትል እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል ወ/ሮ ሰናይት።

‎ዘጋቢ፡ ማርታ ሙሉጌታ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን