ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ሰላማዊ፣ ፍትሐዊና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ የፍትህና የጸጥታ ዘርፍ አመራሮችና ባለሙያዎች ሚና የላቀ መሆኑ ተገለጸ
የጎፋ ዞን ፍትህ መምሪያ የበጀት ዓመቱን የዘጠኝ ወራት የሥራ አፈጻጸምና በቀጣይ የትኩረት መስኮች ዙሪያ ከባለድርሻ አካላት ጋር የውይይት መድረክ አካሂዷል።
የዞኑ ፍትህ መምሪያ ኃላፊ አቶ ደመላሽ ብላቴ፤ በዞኑ ባለፉት ዘጠኝ ወራት የህግ የበላይነትን ለማረጋገጥ፣ ህገ-መንግስቱንና ህገ-መንግስታዊ ስርዓቱን ለማስከበር፣ የዜጎችን ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶችን ለማክበርና መብትና ጊዴታውን የሚያውቅ ህብረተሰብ ለመፍጠር በርካታ ተግባራት ተከናውነዋል ብለዋል።
በልዩ ልዩ ወንጀል ጉዳዩች ከቀረቡ 3 ሺህ 618 መዝገቦች 3 ሺህ 529 መዝገቦች በዐቃቤ ህግ የተለያየ አስተያየትና ውሳኔ የተሰጠ መሆኑን ገልጸዋል።
መምሪያው በሙስና ወንጀሎች እና በታክስና ኢኮኖሚ ወንጀሎች ላይ ልዩ ትኩረት በመስጠት ህጋዊ ውሳኔ እንዲያገኙ የተደረገ ሲሆን በዚህም ሊመዘበር የነበረ ከ11 ነጥብ 7 ሚሊየን ብር በላይ ማዳን ስለመቻሉ አብራርተዋል።
ኃላፊው አያይዘውም ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ሰላማዊ፣ ፍትሐዊና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ የፍትህና የጸጥታ ዘርፍ አመራሮችና ባለሙያዎች ሚና የላቀ መሆኑን ተናግረዋል።
በመምሪያው ታክስና ኢኮኖሚ ወንጀሎች ዋና ስራ ሂደት አስተባባሪ አቶ ደምሴ ዳይዶ እና የሴቶችና ህጻናት ልዩ ምርመራና ክስ ዳይሬክተር አቶ ተፈሪ ትርፌ በጋራ እንደገለጹት፤ የህዝቡን ተጠቃሚነት በማረጋገጥ የፍትህ ተደራሽነትን ለማሳደግ ቅንጅታዊ አሰራርን ማጠናከር እንደሚገባ አስረድተዋል።
ከውይይቱ ተሳታፊዎች መካከል ዋና ኢንስፔክተር ታረቀኝ አጥናፉ፣ አቶ የንገረ የደና እና ኢንስፔክተር ውብነህ ደመላሽ፤ ፈጣንና ቀልጣፋ የፍትህ አገልግሎት ለህብረተሰቡ በመስጠት የሚፈጠሩ ችግሮችን በጋራ ለማረምና ተጠያቂነትን ለማስፈን የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ መክረዋል።
አስተያየት ሰጪዎቹ ግንቦት 24 የሚካሄደው ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ነጻ፣ ዴሞክራሲያዊና ፍትሐዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ የድርሻቸውን እንደሚወጡ አረጋግጠዋል።
ዘጋቢ፡ አይናለም ሰለሞን – ከሳውላ ጣቢያችን

More Stories
ከአየር ንብረት ተፅዕኖ ጋር እየተስተዋሉ ያሉትን ችግሮች ለመከላከል ሁሉም የበኩሉን ሊወጣ እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አካባቢ ጥበቃና የአየር ንብረት ለውጥ ባለስልጣን አስታወቀ
የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ግብርና ቢሮ ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር በክልሉ ለሚገኙ የዘርፉ ባለሙያዎች ስልጠና መስጠት ጀመረ
የቅድመ በሽታ መከላከል ተግባራትን በአግባቡ በመፈፀም ጤናማ ትውልድ ለመፍጠር በሚደረጉ ጥረቶች ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ ተገለፀ