የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የመንግስትን ወጪ ከማዳን ባሻገር ለህሊና እርካታ የሚሰጥ ተግባር መሆኑ ተነገረ

‎በቡርጂ ዞን የ2017 ዓ.ም የክረምት ወራት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ማጠቃለያ መርሃግብር ተካሂዷል።

‎መድረኩን በንግግር ያስጀመሩት በቡርጂ ዞን የማህበራዊ ክላስተር ኃላፊ አቶ ማሙሽ ማነ፤ የበጎ ፈቃድ ሥራ መንግስት ሊያወጣ የነበረውን ወጪ ማዳን ብቻ ሳይሆን የአእምሮ እርካታ መሠረት አድርጎ የሚሠራ ተግባር ነው ብለዋል።

‎የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት አፈፃፀምን አስመልክቶ የቡርጂ ዞን ወጣቶች እና ስፖርት ዩኒት አስተባባሪ አቶ በየነ አሊ፤ የ2017 ዓ.ም የክረምት ወራት በጎ ፈቃድ አገልግሎት አፈፃፀም ሪፖርት ያቀረቡ ሲሆን በ15 ዘርፎች 25 ሺህ 9 መቶ 83 ወጣቶች መሳተፋቸውንና 41 ሺህ 7 መቶ 50 የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ በማድረግ በከተማ ደረጃ መንግስት ሊያወጣ የነበረውን 23 ሚሊዮን 4 መቶ 87 ሺህ 8 መቶ 9 ብር ማዳን መቻሉን አብራርተዋል።

‎በቀረበው የአፈፃፀም ሪፖርት ውይይት የተደረገ ሲሆን በክረምቱ ታቅደው የተከናወኑ ተግባራት መልካም ቢሆኑም በሎጂስቲክ እጥረት ምክንያት አገልግሎት ያላገኙ ቀበሌዎች በቀጣይ ለበጋው የበጎ ፈቃድ ትኩረት ተሰጥቶ ሊሠራ እንደሚገባ ሀሳብ ቀርቧል።

‎ከመድረኩ ተሳታፊዎችም በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት የተሰጣቸውን ተግባር በአግባቡ ለማከናወን አስቸጋሪ ሁኔታዎች እንደነበሩ አንስተው፤ ህብረተሰቡም ሆነ ባለድርሻ አካላት የተግባሩን አስፈላጊነት በመገንዘብ ትኩረት እንዲሰጡበት ጠይቀዋል።

‎በበጎ ፈቃድ ተግባር ወቅት የተሻለ አፈፃፀም ያሳዩ ግለሰቦች እና ተቋማት ሽልማት እና እውቅና አግኝተዋል።

‎በመርሃግብሩ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች፣ በበጎ ፈቃድ አገልግሎት ተሳታፊዎች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተሳትፈዋል።

‎ዘጋቢ: ወርቅአገኘሁ ወልደየስ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን