ታሪክ፣ ባህሎችና ቅርሶችን ጠብቆ ማሳደግ ለቱሪዝም ልማትና ለህዝቦች ትስስር ሚናው ከፍተኛ መሆኑ ተጠቆመ

የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት ቢሮ የ2017 አጠቃላይ የሴክተር ጉባኤና የ2018 በጀት አመት የ1ኛ ሩብ አመት የአፈፃፀም መድረክ በታርጫ ከተማ በመካሄድ ላይ ይገኛል።

በጉባኤው ተገኝተው የመክፈቻ ንግግር ያደረጉ የክልሉ ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት ቢሮ ሀላፊ አቶ ፋንታሁን ብላቴ እንዳሉት፤ ተቋሙ የክልሉን ህዝቦች ባህል፣ ታሪክ፣ ቋንቋ፣ ኪነ ጥበብና ስነ ጥበብ፣ የቱሪዝም ሀብቶችን እንዲሁም የስፖርት ዘርፍ ስራዎችን በማልማት የህብረተሰብ ተጠቃሚነትን የማረጋገጥ ግብ ይዞ እየሰራ ይገኛል።

በተጨማሪም የብዝሃ ማንነትና ባህሎች መገለጫ የሆነው ክልል በውስጡ የያዛቸውን ውብ ባህላዊ እሴቶች ለሥራ ዕድል እና ለገቢ ማግኛ አድርገን አዳብረን ልንጠቀማቸው ይገባል ብለዋል፡፡

ባህል የአንድ ማህበረሰብ የማንነት መገለጫ፣ የገቢ ምንጭ፣ ግጭትን በመከላከል የተረጋጋ ህብረተሰብ እንዲፈጠር እንዲሁም የህብረተሰብ የስነ ልቦና መተሳሰሪያ እንደሆነም አቶ ፋንታሁን አብራርተዋል።

አቶ ፋንታሁን አክለውም፤ ጤናማ፣ ምርታማና በመልካም ስነ ምግባር የታነፀ ዜጋ ለመፍጠር ስፖርት ያለው ሚና የጎላ መሆኑን እና በክልሉ ተተኪ ስፖርተኞችን ለመፍጠር የተጀመሩ የታዳጊ ወጣቶች ፕሮጀክቶችን አጠናክሮ ማስቀጠል እንደሚገባም አሳስበዋል።

በጉባኤው የቢሮው ሀላፊ አቶ ፋንታሁን ብላቴን ጨምሮ ሌሎች የስራ ኃላፊዎች፣ የማኔጅመንት አባላት፣ የስድስቱ ዞኖች የባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ ኃላፊዎች፣ የሁሉም ወረዳዎች የባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት ጽ/ቤት ኃላፊዎች እንዲሁም ሌሎች የባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።

ዘጋቢ፡ እሸቱ ወርቅነህ – ከዋካ ጣቢያችን