ዘንድሮ ለ20ኛ ጊዜ የሚከበረዉን የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀንን አስመልክቶ በተዘጋጀው መሪ ዕቅድ ዙሪያ የዉይይት መድረክ ተካሄደ
“ዴሞክራሲያዊ መግባባት ለህብረብሔራዊ አንድነት” በሚል መሪ ቃል ዘንድሮ ለ20ኛ ጊዜ የሚከበረዉን የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀንን አስመልክቶ በተዘጋጀው መሪ ዕቅድ ዙሪያ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የበዓሉ አብይ ኮሚቴ በቴፒ ከተማ የዉይይት መድረክ አካሂዷል።
በመድረኩ በ19ኛዉ ብሔሮችና ብሔረሰቦች በዓል አከባበር ወቅት የታዩ ጠንካራ ጎኖችን ለማስቀጠልና ክፍተቶችንም ለማረም የሚያስችል መነሻ ሰነድ ቀርቦ ምክክር ተደርጎበታል።
መድረኩን የመሩት የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ አቶ ወንድሙ ኩርታና የክልሉ ብሔረሰቦች ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ አቶ መቱ አኩ እንደገለጹት፤ አምና ላይ በበዓሉ አከባበር ወቅት የታዩ ጠንካራ ጎኖችን ከማስቀጠል በተጨማሪ ዘንድሮ ላይ በአካባቢ ጽዳት፣ በደም ልገሳና በተለያዩ በጎ ተግባራት በአደባባይ በደማቅ ሁኔታ ለማክበር ሁሉም ባለድርሻ አካላት ከወዲሁ ትኩረት ሰጥተው ሊሰሩ ይገባል ብለዋል።
የተከናወኑ ተግባራት ሪፖርትን በአግባቡ ለሚመለከተዉ ማቅረብ እና ቅንጅታዊ አሰራርን እስከታችኛዉ መዋቅር ማጠናከር እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል።
የመድረኩ ተሳታፊዎች በበኩላቸዉ በተሳካ ሁኔታ የዘንድሮዉን በዓል ማክበር እንዲቻል ከሚመለከታቸዉ አካላት ጋር በመሆን የሚጠበቅባቸዉን እንደሚሰሩ ጠቁመዋል፡፡
የዘንድሮዉ የብሔሮችና ብሔረሰቦች ቀን “ዴሞክራሲያው መግባባት ለህብረ ብሔራዊ አንድነት” በሚል መሪ ቃል በክልሉ በታችኛዉ መዋቅር ከህዳር 1 እስከ 18 ቀን እንደሚከበርና በክልል ደረጃ ደግሞ በቤንች ሸኮ ዞን ሚዛን አማን ከህዳር 18 እስከ 20 ቀን 2018 ዓመተ ምህረት ድረስ እንደሚከበር ተገልጿል።
ዘጋቢ፡ ጌትነት ገረመዉ – ከማሻ ጣቢያችን

More Stories
ማሳቸውን ለመኸር እርሻ ደጋግማው በማረስ አለስልሰው በወቅቱ ለመዝራት መዘጋጀታቸውን በከምባታ ዞን ቀዲዳ ጋሜላ ወረዳ ያነጋገርናቸው አንዳንድ አርሶአደሮች ተናገሩ
በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት በተለያዩ የስራ ዘርፎች ከ40 ሺህ በላይ ወጣቶችን ተሳታፊ በማድረግ 46 ሚሊዮን 620 ሺህ ብር በላይ ከመንግሥት ሊወጣ የሚችለውን ለማዳን ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ወጣቶችና ስፖርት ጽ/ቤት አስታወቀ
የቀቤና ልዩ ወረዳ ማህበረሰብ የልማት ፍላጎት ማሟላት የሚቻለው ግብርና ታክስ በታማኝነትና በወቅቱ መክፈል ሲቻል መሆኑ ተገለጸ