የሙስሊሙ ማህበረሰብ አንድነትና ዘላቂ ሠላምን ለማጠናከር በሚከወኑ ተግባራት ተሳትፏቸውን ሊያጠናክሩ እንደሚገባ ተገለፀ
የጂንካ ከተማ አስተዳደር እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ከከተማው ምርጫ አስፈፃሚ ቦርድ ጋር በመሆን በ2017 ዓ.ም የመጅሊሱ ምርጫ በሠላምና በስኬት እንዲጠናቀቅ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት የምስጋናና የዕውቅና ፕሮግራም ተካሂዷል።
የጂንካ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሲሳይ ጋልሺ በመድረኩ ተገኝተው ባስተላለፉት መልክት፤ የሙስሊሙ ማህበረሰብ አንድነትና ዘላቂ ሠላምን ለማጠናከር ላበረከቱት አስተዋጽኦ አመስግነው ይህንን በጎ ተግባር አዲስ ከተመረጡ አመራሮች ጋር በመሆን አጠናክረው እንዲቀጥሉም አሳስበዋል።
የጂንካ ከተማ ሠላምና ፀጥታ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ መላኩ አበራ እና የከተማው ፖሊስ አዛዥ ምክትል ኮማንደር ካሌብ ከብትመር፤ የመጅሊስ ምርጫው በሠላም እንዲጠናቀቅ በትኩረት መሠራቱን አንስተው የሙስሊሙ ማህበረሰብ ሠላምና አንድነትን በማጠናከር ከመንግስት ጎን በመሆን ለጋራ ልማትና ብልፅግና የድርሻቸውን እንዲወጡም ጥሪ አቅርበዋል።
የኣሪ ዞን እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ ጀማል ሙሀመድ እና የጂንካ ከተማ አስተዳደር እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ኃላፊ አቶ ኡሚሬድን ግርማ የመድረኩን ዓላማ ገልፀው ሁለንተናዊ ዕድገትና ዘላቂ ሠላምን ለማስፈን አዲስ ከተመረጡ አባላት ጋር በቅንጅት እንደሚሠሩም ገልፀዋል።
በቀጣይ አምስት አመታት በልማት፣ በሠላምና አንድነትን ይበልጥ የሚያጠናክሩ ተግባራትን በማከናወን የተጣለባቸውን ኃላፊነት በታማኝነትና በአግባቡ ለመወጣት መዘጋጀታቸውን አዲስ የተመረጡ አባላት ተናግረዋል።
የጂንካ ከተማ አስተዳደር እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ከከተማው ምርጫ አስፈፃሚ ቦርድ ጋር በመሆን በ2017 ዓ.ም የመጅሊሱ ምርጫ በሠላምና በስኬት እንዲጠናቀቅ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላትና ከዚህ በፊት ላገለገሉ አመራሮች የምስጋናና የዕውቅና ሽልማት በመስጠት መድረኩ ተጠናቋል።
ዘጋቢ፡ ተመስገን አሰፋ – ከጂንካ ጣቢያችን

More Stories
የአርብቶ አደሩን ማህበረሰብ በመንገድ መሠረተ ልማት ተጠቃሚ ለማድረግ እየሰራ መሆኑን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መሰኖና ቆላማ አካባቢዎች ልማት ቢሮ አሰታወቀ
ሳውላ ከተማን ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም ምቹ የማድረግ የ5 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ሥራ እየተካሄደ ነው
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የቱሪዝም ሀብቶችን በማልማትና ሰላምን በማጽናት ማህበረሰቡን ተጠቃሚ የማድረግ ሥራ ተጠናክሮ ቀጥሏል