ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ኢትዮጵያ በራስ አቅም ጀምራ መጨረስን ያሳየችበት ዳግማዊ የአድዋ ድል የሆነ እና የወል ትርክትን ያፀና ፕሮጀክት መሆኑን የእኖር ወረዳ አስተዳደር ገለጸ

ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ኢትዮጵያ በራስ አቅም ጀምራ መጨረስን ያሳየችበት ዳግማዊ የአድዋ ድል የሆነ እና የወል ትርክትን ያፀና ፕሮጀክት መሆኑን የእኖር ወረዳ አስተዳደር ገለጸ

የወረዳው ነዋሪዎች በበኩላቸው ግድቡ ከበርካታ ፈተናዎች በኋላ ለምረቃ በመብቃቱ መደሰታቸውን ገልጸዋል።

ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ በኢትዮጵያዊያን የተባባረ ክንድ ተገንብቶ ብርሃን ሊሰጥ መጋቢት 24 ቀን 2003 ዓ.ም የመሰረት ድንጋይ መቀመጡ ይታወሳል፡፡

አባይ ለዘመናት ለኢትዮጵያ የረባ ጥቅም ሳይሰጥ ወደ ጎሮቤት አገራት የሚሰደድ፣ የሚታይ እንጂ የማይበላ እንጀራ ሆኖ መቆየቱም የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡

በጉራጌ ዞን የእኖር ወረዳ አስተዳደር ጽ/ቤት ሃላፊ አቶ ምትኩ ሃይለማሪያም ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ኢትዮጵያ በራስ አቅም ጀምራ መጨረስን ያሳየችበት ዳግማዊ የአድዋ ድል የሆነ እና የወል ትርክትን ያፀና ፕሮጀክት መሆኑን ገልጸዋል።

ለዚህ መሳካት የወረዳው ህዝብ ከፍተኛ አስተዋጽኦ በማድረግ ተሳትፎውን በተግባር ያረጋገጠበት ነውም ብለዋል ሃላፊው።

በቀጣይም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት ሊሰሩ የታሰቡ ትላልቅ ሃገራዊ ፕሮጀክቶችን በመደገፍ ነዋሪዎች የራሳቸውን ሚና መወጣት እንደሚገባቸው አሳስበዋል።

‎የህዳሴው ግድብ ኢትዮጵያዊያንን በአንድነት ያስተሳሰረ ጠንካራ ፕሮጀክት መሆኑን በማንሳት የለውጡ መንግስት በርካታ ውጫዊና ውስጣዊ ጫናዎችን በመቋቋም ለድል ያበቃበት ትልቅ ስኬት ነው ብለዋል።

በዚህም የወረዳው ነዋሪዎች ከበርካታ ፈተናዎች በኋላ ግድቡ ለምርቃት በመብቃቱ መደሰታቸውን ተናግረዋል።

ከገጠር እስከ ከተማ፣ ከደሃ እስከ ሃብታም፣ ከህጻን እስከ ሽማግሌ፣ ከምሁሩ እስከ አልተማረው እንዲሁም በውጪ አገራት የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ከእለት ጉርሳቸው ቀንሰው በማዋጣት በተባበረ ክንድ እንደ ዓይን ብሌናቸውም ሲጠባበቁት ለስኬት የበቃ እንደሆነም አስተያየት ሰጪዎቹ አክለዋል።

ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የህዝቡ ተሳትፎ የአይቻልም ስሜትን የቀየረ የጋራ ሃብት በመሆኑ በቀጣይም ሃገራችን በምታከናውናቸው የልማት ስራዎች ድጋፋቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል።

ዘጋቢ፡ አስቻለው አማረ – ከወልቂጤ ጣቢያችን