በኧሌ ዞን ኮላንጎ ከተማ ከ165 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የኮላንጎ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ግንባታ ማስጀመሪያ መርሐ ግብርም ተካሄደ
ሀዋሳ፣ መስከረም 08/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በኧሌ ዞን ኮላንጎ ከተማ ከ165 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የኮላንጎ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ግንባታ ማስጀመሪያ መርሐ ግብርም ተካሄዷል፡፡
የሆስፒታሉ ግንባታ ሕብረተሰቡ በጤናው ዘርፍ የሚያነሳቸውን የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ሊፈታ የሚችል መሆኑን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ አስታወቋል።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ ተወካይ እና የጤና ልማት እቅድና ኢኮኖሚ አስተዳደር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ተገኝ ጮቴ እንደገለፁት ቢሮው የክልሉን የጤና ሽፋንና የአገልግሎት ተደራሽነት በማሳደግ የእናቶችና የሕፃናትን ሞት ለመታደግ እየሠራ መሆኑን ተናግረው የዚሁ አካል የሆነው የኮላንጎ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ግንባታን ናታሊያ ከተሰኘ የግንባታ ተቋራጭ ጋር ከ165 ሚሊዬን 345 ሺህ ብር በላይ በሆነ ወጪ ውል በመግባት ሥራ ማስጀመሩን አስረድተዋል።
የኧሌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አርሻሌ አርካሌ እና የዞኑ ጤና ዪኒት አስተባባሪ አቶ ዘመኑ ዘንዳኦ በጋራ እንደገለፁት የኮላንጎ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ግንባታ መጀመሩ በጤናው ዘርፍ የማህበረሰቡን የቆየ የመልካም አስተዳደር ችግርን እንደሚቀርፍ ገልፀው በግንባታው ሂደት አስፈላጊው ድጋፍና ክትትል ይደረጋል ብለዋል።
የናታሊያ ግንባታ ተቋራጭ ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ወንድማገኝ በቀለ በበኩላቸው በማህበረሰቡ ስለተደረገው አቀባበል አመስግነው ግንባታውን በጥራትና በአጭር ጊዜ ውስጥ በማጠናቀቅ ለአገልግሎት እንዲበቃ ሁለንተናዊ ጥረት ይደረጋል ብለዋል።
በአቅራቢያቸው ሆስፒታል ባለመኖሩ የተሻለ ሕክምና ለማግኘት ረጅም መንገድ ተጉዘው ለአላስፈላጊ ወጪ እና እንግልት ይዳረጉ እንደነበር አስታውሰው መንግስት ይህንን ችግር ለመቅረፍ የሆስፒታል ግንባታ በማስጀመሩ መደሰታቸውን ነዋሪዎች ገልጸዋል ።
ዘጋቢ፡- ተመስገን አሰፋ ከጂንካ ጣቢያችን

More Stories
የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ እና የአደረጃጀት ዘርፍ የ2018 በጀት አመት አፈጻጸምና የ2019 በጀት ዕቅድ ዙሪያ በታርጫ ከተማ ውይይት እየተካሄደ ነው
ኦሞ ባንክ ሳውላ ዲስትሪክት በ2018 በጀት ዓመት ከ86 ሚሊዮን ብር በላይ የተጣራ ቁጠባ ማስመዝገቡን ገለጸ
እየተካሔደ ያለው ሀገራዊ ምክክር በሀገሪቱ አንድነት እና ሠላም ለማስፈን ፋይዳው የጎላ መሆኑን የአርባምንጭ ከተማ ነዋሪዎች ተናገሩ