በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ቡርጂ ዞን “በህብረት ችለናል” በሚል መሪ ቃል ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ በድል ተጠናቆ መመረቁን አስመልክቶ ዞናዊ የፓናል ዉይይት መድረክ ተካሄደ

‎በመድረኩ ላይ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የቡርጂ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዳኜ ህዶ፤ ኢትዮጵያ በግድቡ ላይ ከውስጥም ከውጭም እየተነሱ የነበሩ ተግዳሮቶችን ተጋፍጣ ግንባታውን በማጠናቀቋ እንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል።

‎እንደ ኢትዮጵያ ብዙ ፕሮጀክቶችን አሳክተናል ያሉት ዋና አስተዳዳሪው፤ በዞኑ እየመጡ ያሉ ለውጦች ቢኖሩም ገና ብዙ የሚቀር በመሆኑ ሁሉም የዞኑ ነዋሪዎች እጅ ለእጅ ተያይዘዉ እንዲሠሩም አሳስበዋል።

‎የቡርጂ ዞን ብልጽግና ፓርት ቅንርጫፍ ጽ/ቤት ሃላፊ አቶ ኡሜ ቾኮል በበኩላቸው፤ የህዳሴ ግድብ በብዙ ተፅዕኖ አልፎ ሁሉም የኢትዮጵያ ህዝብ ባደረገው ርብርብ የተጠናቀቀ ፕሮጀክት በመሆኑ ልንኮራ ይገባል ብለዋል።

‎አክለውም በህብረት ከተሰለፍን የትኛውንም ተግባር በራሳችን አቅም መሥራት እንደምንችል ማሳያ መሆኑን ተናግረዋል።

‎በመረድኩ በቀረበው መነሻ ጽሑፍ ላይ የአባይ ወንዝ ታሪካዊ ዳራ፣ በህዳሴ ግድብ ግንባታ ሂደት የነበሩ ልዩ ልዩ ተግዳሮቶች እና የህዳሴ ግድብ አንደምታዎች ላይ ገለፃ ተደርጎ ውይይት ተደርጓበታል።

‎የመድረኩ ተሳታፊዎችም ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ከዘመናት ቁጭት የወጣንበት፣ የአላማ ፅናት ያሳየንበት እና በህብረት መቻላችንን ያረጋገጥንበት የዚህ ትውልድ አድዋ መሆኑን ጠቅሰው፤ የዞኑ ህዝብም ከዚህ ትምህርት በመውሰድ የተጀመሩ ፕሮጀክቶችን በጋራ ለድል ማብቃት እንዳለበትና በትምህርት ጥራት ላይም መድገም እንደሚያስፈልግ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

‎ዘጋቢ: ቦጋለ ሉሳ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን