በጎፋ ዞን “ከግድቡ ወደ ወደብ ” በሚል መሪ ቃል የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ መጠናቀቅን በማስመልከት የፓናል ዉይይት ተካሂዷል።
በውይይቱ ላይ በሳወላ ከተማ ከሚገኙ የክልል ተቋማት፣ የሳውላ ከተማ አስተዳደር፣ ዙሪያ ወረዳ አመራሮች እና ባለሙያዎች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው አካላት ተሳትፈዋል፡፡
የጎፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ኢንጂነር ዳግማዊ አየለ፤ የህዳሴውን ግድብ እኛ ኢትዮጵያዊያን በራሳችን አቅም በመገንባታችን ከእኛ አልፎ ለአፍሪካዊያን የኩራት ምንጭና ከአይችሉም መንፈስ ወጥተን መቻላችንን ያረጋገጥንበት የትውልድ አሻራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያን ጂኦግራፊያዊ አቀማመጥ መነሻ በማድረግ የዜጎችን ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ አኳያ በርካታ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸው፤ ባለፉት ጊዜያት ሀገር የመሩ መንግስታት የሞከሩት በአሁኑ መቻላችን ትልቅ አቅም መሆኑን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ፍትህ ቢሮ ምክትልና የወንጀልና የፍትሐብሔር ዘርፍ ኃላፊ አቶ አድማሱ መንግሥቱ ተናግረዋል፡፡
በዚህም ከተከናወኑ ተግባራት መካከል የህዳሴው ግድብ ዋነኛው ሲሆን ኢትዮጵያ የተከፈተባትን ሁሉን አቀፍ ጦርነትና ዘመቻ ተቋቁማ ታላላቅ ድሎችን ማስመዝገብ እንደምትችል ያስመሰከረችበት ነው ብለዋል።
የሣውላ ከተማ ከንቲባ ዶክተር ንጉሴ መኮንን በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ኢትዮጵያ የዓለም የጥቁር ህዝቦች የእኩልነት መገለጫ፣ የአፍሪካ ተምሳሌትና የአይበገሬነት ማሳያ መሆኗን ጠቅሰው ግድቡ ከኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታው ባሻገር የቅኝ ግዛት ትርክትን የሰበረ የዚህ ትውልድ ዳግማዊ አድዋ ነው።
የውይይቱ ተሳታፊዎች የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ከኢትዮጵያውያን አልፎ ለመላው አፍሪካውያን የይቻላል ምልክት ማሳያ አርማ የሆነበት ፤ ወደ ባህር በር ሥራ የምንሰማራበት ነው ብለዋል፡፡
ዘጋቢ፡ ስንታየሁ ሙላቱ – ከሳውላ ጣቢያችን

More Stories
ምክር ቤቱ በጋሞ ዞን ጉዳት ለደረሰባቸው ወገኖች የ3 ሚላዮን ብር ድጋፍ አደረገ
የንጹህ መጠጥ ውሃ ችግር ለመቅረፍ የሚያስችሉ ፕሮጀክቶች በመጠናቀቅ ላይ እንደሚገኙ የበና ጸማይ ወረዳ አስተዳደር አስታወቀ
በክልሉ ከቱሪዝሙ ዘርፍ ባለፉት 9 ወራት 925.6 ሚሊዮን ብር ተገኝቷል