ታላቁ የህዳሴ ግድብ ተጠናቆ መመረቅን ምክንያት በማድረግ የይርጋጨፌ ወረዳ እና ከተማ አስተዳደር በጋራ በመሆን የድጋፍ ሰልፍ አካሄዱ
በጌዴኦ ዞን ይርጋጨፌ ወረዳ እና ከተማ አስተዳደር በጋራ በመሆን “በህብረት ችለናል” በሚል መሪ ቃል ነው የድጋፍ ሰልፉ የተካሄደው።
በድጋፍ ሰልፉ ላይ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የይርጋጨፌ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ታደለ ጥላሁን፤ ግድባችን ከውስጥም ሆነ ከውጪ ሀይሎች ሲደርስበት የነበረውን ጫና በመቋቋም አይችሉም የተባለውን ፕሮጀክት በህብረት ሆነን ማጠናቀቅ በመቻላችን እንኳን ደስ አለን ሲሉ ተናግረዋል።
የባህር በር ጥያቄ ቅንጦት አይደለም ያሉት አቶ ታደለ፤ ቀጣይ ይህን ፕሮጀክት እውን ለማድረግ ዜጎች ከመንግስት ጎን በመሆን የተለመደውን ትብብር ሊያደርጉ ይገባል ሲሉም ጥሪ አቅርበዋል።
ሌላኛው በድጋፍ ሰልፉ ላይ መልዕክት ያስተላለፉት የይርጋጨፌ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዳዊት ቡኔ፤ የፀጥታው ምክር ቤት ጫና ሲያሳድርብን በአንድነት ተቋቁመን በመንግስታችን ግንባር ቀደም አስተባባሪነት መጨረስ ችለናል ብለዋል።
በወረዳውም ሆነ በከተማው እየተከናወኑ ያሉትን የልማት ስራዎች በአንድነት መንፈስ አጠናክረን ልናስቀጥል ይገባል ሲሉም ጥሪ አቅርበዋል።
በድጋፍ ሰልፉ ላይ ከተሳተፉት መካከል አቶ ክፍለ ጅክሶ እና አቶ አክሊሉ መኩሪያ፤ በግድቡ መጠናቀቅ ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማቸው ገልፀው ለቀጣይ ሀገራዊ ፕሮጀክቶች ከመንግስት ጎን እንደሚሆኑ ተናግረዋል።
በበድጋፍ ሰልፉ ላይ የተለያዩ መፈክሮች የተሰሙ ሲሆን “ከግድብ ወደ ወደብ”፣ “ግድባችን የአንድነታችን አርማ ነው”፣ “አባይ ዳግማዊ የአድዋ ድል ነው”፣ “ግድቡ የአንድነታችን እና የአብሮነታችን አርማ ነው”፣ “የባህር በሩንም በአንድነት እናሳካለን” የሚሉት ተጠቃሾች ናቸው።
ዘጋቢ: ወርቅአገኘሁ ወልደየስ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን
ታላቁ የህዳሴ ግድብ ተጠናቆ መመረቅን ምክንያት በማድረግ የይርጋጨፌ ወረዳ እና ከተማ አስተዳደር በጋራ በመሆን የድጋፍ ሰልፍ አካሄዱ

More Stories
የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ እና የአደረጃጀት ዘርፍ የ2018 በጀት አመት አፈጻጸምና የ2019 በጀት ዕቅድ ዙሪያ በታርጫ ከተማ ውይይት እየተካሄደ ነው
ኦሞ ባንክ ሳውላ ዲስትሪክት በ2018 በጀት ዓመት ከ86 ሚሊዮን ብር በላይ የተጣራ ቁጠባ ማስመዝገቡን ገለጸ
እየተካሔደ ያለው ሀገራዊ ምክክር በሀገሪቱ አንድነት እና ሠላም ለማስፈን ፋይዳው የጎላ መሆኑን የአርባምንጭ ከተማ ነዋሪዎች ተናገሩ