መረጃ ለአንድ ሀገር ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ሚናው የጎላ መሆኑ ተገለጸ
ሀዋሳ፡ መስከረም 05/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) መረጃ ለአንድ ሀገር ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ሚናው የጎላ መሆኑን የኢትዮጵያ ስታስቲክስ አገልግሎት አስታወቀ
አገልግሎቱ ለመጀመሪያ ጊዜ ለሚካሄደው የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ ለመስክ መረጃ ሰብሳቢዎች እና ተቆጣጣሪዎች በቦንጋ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ስልጠና እየተሰጠ ነው።
በስልጠናው የተገኙት በኢትዮጵያ ስታስቲክስ አገልግሎት የፌደራል ስልጠና አስተባባሪ አቶ ካሳሁን መኩሪያ፥ በሳይንሳዊ ዘዴዎች የተሰበሰቡ መረጃዎች የአንድን ሀገር ኢኮኖሚያዊ እና ዴሞክራሲያዊ ልማት ለማፋጠን ሚናቸው የጎላ ነው ብለዋል።
ሀገራዊ የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ ለማካሄድ በ55 የስልጠና ማዕከላት ለባለሙያዎች ስልጠና እየተሰጠ መሆኑን ተናግረው በቦንጋም ማዕከል የተጀመረው የዚሁ አካል እንደሆነ ጠቁመዋል።
በሁሉም ማዕከላት 43 ሺህ ሰልጣኞች ስልጠናውን እየወሰዱ መሆናቸዉን ጠቁመው ፤ ከስልጠናው በሚያገኙት ክህሎት መሠረት መረጃ ለመሰብሰብ ይሰማራሉ ብለዋል።
በቦንጋ የስልጠና ማዕከል ከካፋ ዞን ሁሉም ወረዳዎችና ከተማ አስተዳደሮች የተመለመሉ ሰልጣኞች እየተሳተፉ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በኢትዮጵያ ስታስቲክስ አገልግሎት የቦንጋ ስልጠና ማዕከል አስተባባሪ አቶ ሀብታሙ ካውሳ ናቸዉ።
የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ ሀገራዊ ጠቀሜታው የጎላ በመሆኑ ሰልጣኞች በአግባቡ ተከታትለው ተግባራዊ ማድረግ እንዳለባቸውም አስገንዝበዋል።
የቦንጋ ስልጠና ማዕከል የቴክኒክ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ተመስገን ጎሹ በበኩላቸው በቦንጋ ማዕከል 236 ሰልጣኞች እየሰለጠኑ መሆኑን ተናግረዋል።
ሰልጣኞች ስልጠና ካጠናቀቁ በኋላ በከተማና በገጠር በተለያዩ ስራ ዘርፎች የተሰማሩ ድርጅቶች ጋር በመድረስ መረጃ ይሰበስባሉ ብለዋል።
የካፋ ዞን ስራና ክህሎት መምሪያ ኃላፊ አቶ ሚልዮን ኃይሌ፥ ሰልጣኞች መረጃ ለመሰብሰብ ወደ መስክ በሚሰማሩበት ወቅት ታዓማኒ መረጃ መሰብሰብ እንዳለባቸው አስገንዝበው ለዚህም ዞኑ ድጋፍና ክትትል እንደሚያደርግም ገልጸዋል።
የቦንጋ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ምክትል ዲን ወይዘሮ ለጢፋ አህመድ በበኩላቸው ሰልጣኞች በስልጠና ቆይታቸው የሚያስፈልጋቸውን ድጋፍ ኮሌጁ ያደርጋል ብለዋል።
የስልጠናው ዓላማ ሀገራዊ የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ ለማካሄድ የባለሙያዎች አቅም ማጎልበት መሆኑም ተገልጿል።
ዘጋቢ: ሀብታሙ ኃይሌ – ከቦንጋ ጣቢያችን

More Stories
የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ እና የአደረጃጀት ዘርፍ የ2018 በጀት አመት አፈጻጸምና የ2019 በጀት ዕቅድ ዙሪያ በታርጫ ከተማ ውይይት እየተካሄደ ነው
ኦሞ ባንክ ሳውላ ዲስትሪክት በ2018 በጀት ዓመት ከ86 ሚሊዮን ብር በላይ የተጣራ ቁጠባ ማስመዝገቡን ገለጸ
እየተካሔደ ያለው ሀገራዊ ምክክር በሀገሪቱ አንድነት እና ሠላም ለማስፈን ፋይዳው የጎላ መሆኑን የአርባምንጭ ከተማ ነዋሪዎች ተናገሩ