ለጠቅላላ አገራዊ ምርት ግምት መሠረታዊ መረጃዎችን ለመሰብሰብ ለሚደረገው ጥረት ሁሉም የድርሻውን እንዲወጣ ተጠየቀ
ሀዋሳ፡ መስከረም 05/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) ለጠቅላላ አገራዊ ምርት ግምት መሠረታዊ መረጃዎችን ለመሰብሰብ በሚደረገው ጥረት ላይ ሁሉም የድርሻውን እንዲወጣ የዳዉሮ ዞን አስተዳደር አስታወቀ፡፡
በኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት የሶዶ ስታቲስቲክስ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ከመስከረም 5 ጀምሮ ለሚቀጥሉት 20 ቀናት የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ ከዳዉሮና ኮንታ ዞኖች ለተወጣጡ ባለሙያዎችና አመራሮች ስልጠና እየሰጠ ነው።
የዳዉሮ ዞን ዋና አስተዳደር ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ወንድሙ ወራቦ እንደገለፁት ትክክለኛና ተጨባጭ መረጃ ለአገር ከሚሰጠው ፋይዳ አኳያ ኃላፊነት የሚጠይቅ የልማትና የኢኮኖሚ አቅጣጫ እንዲወስኑ የሚያግዝ በመሆኑ በአገር ደረጃ በቁርጠኝነትና በጥብቅ ዲስፕሊን እየተሠራ ይገኛል።
ይህ የመረጃ አሰባሰብ ሥርዓት ውጤታማ ለማድረግ በተገቢው የሰው ኃይል በማደራጀት በክህሎትና በቴክኖሎጂ እንዲታገዝ የሚያስችል ሥራም በትኩረት እየተሠራ መሆኑን አመላክተዋል።
ለጠቅላላ አገራዊ ምርት ግመታ ተጨባጭ መረጃ እንዲኖር መሠረታዊ መረጃዎችን ለማስገኘት የሚደረገው ጥረት የመስክ ባለሙያዎች በኃላፊነት እንዲሠሩም ጠይቀዋል።
የዞኑ ሥራና ክህሎት መምሪያ ኃላፊ አቶ ባቲሣ ዋጌሾ በበኩላቸው ባለሙያዎች በአገራዊ አጀንዳና ለአገራዊ ኢኮኖሚ ዕድገት የድርሻቸውን ሊወጡ የሚችሉ የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ ላይ ሰልጣኞች በኃላፊነት የተጣለባቸውን ተግባር መወጣት ይገባል ብለዋል።
በወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ ዳዉሮ ታርጫ ካምፓስ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ እንግዱ ካሱ በበኩላቸው ለትክክለኛ አገራዊ ፖሊሲ የሚጠቅሙ መረጃዎችን በመሰብሰብና በማደራጀት በኩል እየተደረገ ያለው ተግባር ውጤታማ እንዲሆን በተቀናጀ ጥረት ሊሠራ ይገባል፡፡
አሁን ላይ ሰልጣኞች የተጣለባቸውን ኃላፊነት በመረዳት ለቀጣይ አገራዊ ኢኮኖሚ የሚጠቅሙ ተግባራትን ማከናወን ይጠበቅባቸዋል ብለዋል።
በቀጣይ ለሚከናወኑ ተግባራት የሚያግዙ ድጋፎች በተቀናጀ ሁኔታ እንደሚደረጉም የሥራ ኃላፊዎች ገልጸዋል።
የሶዶ ስታቲስቲክስ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ደርዘኔ ደግፌ በበኩላቸው ስልጠናው ለሚቀጥሉ 20 ቀናት የሚሰጥ በመሆኑ ሰልጣኞች በዲስፕሊን እንዲከታተሉም ጠይቀዋል።
እንደአገር ከ55 ሺህ በላይ የቆጠራ ጣቢያዎች ሲኖሩ በ55 የሥልጠና ጣቢያዎች ከ40 ሺህ በላይ የመስክ ባለሙያዎች ሥልጠናውን የሚካፈሉ ሲሆን እንደ ዳዉሮና ኮንታ በአንድ የሥልጠና ማዕከል 245 ስልጠኞች ስልጠናውን የሚወስዱ ይሆናል።
ዘጋቢ፡ መሣይ መሠለ – ከዋካ ጣቢያችን

More Stories
የእናቶችንና ጨቅላ ህፃናትን ሞት ለመቀነስ በሚደረጉ ጥረቶች ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ ተገለፀ
የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርእሰ መስተዳደር (ዶ/ር ) እንዳሻው ጣሰው በተገኙበት በጉራጌ ዞን ወልቂጤ ከተማ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ምርቃትና የመሰረተ ድንጋይ የማስቀመጥ ስነ-ስረዓት እየተካሄደ ይገኛል
በጎፋ ዞን ሳውላ ከተማ የምግብ ዋስትና ፕሮጀክት እየተስተዋለ ያለውን ድህነት እና የስራ አጥነት ችግር ለመቅረፍ ያበረከተው አስተዋጽኦ የላቀ መሆኑ ተገለጸ