ጳጉሜን 1 – የጽናት ቀን “ጽኑ መሠረት ብርቱ ሀገር” በሚል መሪ ቃል በካፋ ዞን ቦንጋ ከተማ እየተከበረ ነው።
በመድረኩ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የካፋ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የገቢዎች መምሪያ ኃላፊ አቶ ደመላሽ ንጉሴ፤ ሀገራዊ ለውጥ ከመጣ ወዲህ በተለያዩ ስያሜዎች የጳጉሜን ወር ማክበር እየተለመደ መጥቷል ብለዋል።
ኢትዮጵያ በርካታ ችግሮችን ተሻግራ በኢኮኖሚ፣ በፖለቲካና በማህበራዊ ዘርፍ የተመዘገቡ ስኬቶችን በማሰብ የተሻለ ነገን መፍጠር ላይ ማተኮር እንደሚገባ ገልጸዋል።
የዘንድሮው የጳጉሜ ወር የህዳሴ ግድብ መጠናቀቅ የሚበሰርበት ወቅት መሆኑ ልዩ ያደርገዋል ያሉት አቶ ደመላሽ፤ የዚህ ድል ባለቤት በመሆናችን እንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል።
ጳጉሜን 1 የጽናት ቀኑ ተብሎ የመከበሩ ዋና ምክንያት ጽናት ለሀገር ሁለንተናዊ ለውጥ መሠረት በመሆኑ ነው ብለዋል።
በጽናት የሚቆም ትውልድ ሀገርን በመገንባት ቀጣይነትን እንደሚያረጋግጥ ተናግረዋል።
በጽናት የሚቆም ትውልድ በአቋም በመታገል ለሀገር ቅድሚያ ይሰጣል ብለዋል።
የጽናት ቀን ሲከበር ለኢትዮጵያ ለሰላምና ለደህንነት የታገሉና የተዋደቁትን በማሰብና በማመስገን ሊሆን እንደሚገባ አሳስበዋል።
በመድረኩ ዕለቱን በተመለከተ የመወያያ ሰነድ ያቀረቡት የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ሰብስቤ ሻዎኖ በበኩላቸው፤ ጽናት ከግለሰብ እንደሚጀምር ጠቁመው የጸና ቤተሰብ የጸናች ሀገር ለመገንባት ወሳኝ ነው ብለዋል።
ፈተናዎችን ተሻግሮ ሀገርን ለትውልድ ለማስረከብ ጸንቶ መቆምን እንደሚጠይቅ አንስተዋል።
ዘጋቢ፡ ሀብታሙ ታደሰ – ከቦንጋ ጣቢያችን

More Stories
የሰራተኞች የገንዘብ ቁጠባ እና ብድር ኅብረት ሥራ ማህበር ብዙዎችን የቤት ባለቤት ማድረጉ ተገለጸ
በሁሉም ዘርፎች እንደሀገር አመርቂ ውጤቶች እየተዘመገቡ ነው – የቦንጋ ከተማ ነዋሪዎች
የወሳኝ ኩነት ምዝገባ ስርዓትን በማዘመን የመረጃ ታማኝነትን ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑ ተገለጸ