ሀገራችንን ወደ ብልፅግና ለማድረስ የጽናት መንፈሳችንን ማደስ እንደሚገባ ተገለጸ

“ጽኑ መሰረት ብርቱ ሀገር” በሚል መሪ ቃል ጳጉሜን 1 ‘የጽናት ቀን’ በጎፋ ዞን በተለያዩ ዝግጅቶች ተከብሯል።

የሣውላ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ዶ/ር ንጉሴ መኮንን፤ ከለውጡ ማግስት ሀገራችን ኢትዮጵያ በርካታ ችግሮች ቢያጋጥሟትም ባለፉት ሰባት ዓመታት በጽናት በመታገል በርካታ ድሎች ማስመዝገቧን ተናግረው በቀጣይ በከተማው የተጀመሩ የልማት ሥራዎች በጽናትና በአንድነት የምንተገብርበት መሆኑን ገልፀዋል፡፡

በዕለቱን መልዕክት ያስተላለፉት የጎፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ኢንጂነር ዳግማዊ አየለ፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድባችን ለምረቃ ጥቂት ቀናት በቀረበት ወቅት የጽናት ቀን መከበሩ ደስታችንን እጥፍ ያደርገዋል ብለዋል፡፡

ግድቡ የሀገር ኩራት ምልክት፣ የህዝቡ የጽናት ማሳያ መሆኑን ገልጸው እንደ ዞን ከለውጡ ማግስት ወዲህ የነበሩ ችግሮችን በመፍታት በአካባቢያችን የተጀመሩ መሰረተ ልማቶችና በኢኮኖሚው ዘርፍ የተመዘገቡ ለውጦች የአንድነትና የጽናት ውጤት እንደሆኑም ተናግረዋል፡፡

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ፍትህ ቢሮ ኃላፊና የሣውላ ክላስተር አስተባባሪ አቶ አቤነዘር ተረፈ፤ አባቶቻችን ትላንት አደዋ ላይ ድል ያደረጉበትን ዛሬ በአንድነት እና በጽናት በልማት ሥራዎቻችን በመድገም በክልላችን የተመዘገቡ ውጤቶችና ስኬቶች የፅናታችን መገለጫ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

በመርሃ ግብሩ የተለያዩ የፖሊስ ትዕይቶችና የኢትዮጵያ ብሔራዊ የህዝብ መዝሙር ቀርቦ ተጠናቋል።

ዘጋቢ: ስንታየሁ ሙላቱ – ከሳውላ ጣቢያችን