የአቅም ደካማ ወገኖችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን ለመቅረፍ በጎ ተግባራትን ማጠናከር እንደሚገባ ተገለፀ

የአቅም ደካማ ወገኖችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን ለመቅረፍ በጎ ተግባራትን ማጠናከር እንደሚገባ ተገለፀ

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ በኣሪ ዞን በተለያዩ ወረዳዎችና ጂንካ ከተማ “በጎነት ለኢትዮጵያ ከፍታ” በሚል መሪ ቃል በሚካሄድ የአንድ ጀምበር የአረጋውያን አዲስ ቤት ግንባታና ዕድሳት መርሐ ግብር አስጀምሯል።

የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የአቅመ ደካሞችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ሰው ተኮር ስትራቴጂ መሆኑም ተመላክቷል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ እንዳሻው ሽብሩ፤ የአንድ ጀምበር ቤት ግንባታውን በይፋ ባስጀመሩበት ወቅት፤ ቢሮው የበጎ ፍቃድ አገልግሎት በተለያዩ ዘርፎች እያከናወነ መሆኑን አንስተው ህብረተሰቡን ተጠቃሚ በሚያደረጉ ጤናና ጤና ነክ እንዲሁም የመረዳዳት እሴቶች ባህል የሚያደርግና ከመንግስት ይወጣ የነበረ ከፍተኛ ሀብት በማዳን ጭምር ለበርካታ አቅም ደካማ ማህብረሰብ ክፍሎች የቤት ግንባታ እንደሚካሄድ ተናግረዋል።

አቶ እንደሻዉ አክለውም፤ የመረዳዳትና የመደጋገፍ ባህላችንን በማጠናከር ሰው ተኮር ተግባራትን በማከናወን የተሻለች ኢትዮጵያ መገንባት እንደሚገባ አሳሰበዋል።

የኣሪ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብርሃም አታ የአንድ ጀምበር የአቅመ ደካማ ቤት ግንባታ የበጎ ተግባር አገልግሎት የህሊና እርካታን የሚሰጥ ከመሆኑም በላይ በችግር ውስጥ ያሉ አቅመ ደካማ ወገኖችን ህይወት የሚቀይር ተግባር ነው ብለዋል።

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊና የምግብና የመድኃኒት የጤና የአገልግሎቶች ጥራት ቁጥጥር ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ዮሴፍ ሶንቆ፤ ቢሮው በክልሉ ውስጥ ባሉ መዋቅሮች ውስጥ የአረጋውያን ቤት ግንባታ በተቋሙ ሠራተኞችና አመራሩ ትብብር እንደሚካሄድ ጠቁመው በዛሬው ዕለት በኣሪ ዞን በደቡብ ኣሪ፣ በበካ ደውላና በጂንካ ከተማ አስተዳደር በይፋ መጀመሩን ተናግረዋል።

የአንድ አረጋውያን ቤት ግንባታ ከ350 ሺህ ብር ወጪ ሊያወጣ የሚችል ነው ያሉት ምክትል የቢሮ ኃላፊው፤ በሁሉ አቅፍ ትብብር የቤት ግንባታውን ለማሳካት ጥራት ይደረጋል ብለዋል።

በበጎ ፈቃድ አገልግሎት ተጠቃሚ የሆኑ የማህበረሰብ ክፍሎችም በተጀመረው ቤት ግንባታ ሂደት መደሰታቸውን ገለጸዋል።

ዘጋቢ: ጄታ ታገሠ – ከጂንካ ጣቢያችን