ተማሪዎች በወቅቱ ትምህርት ቤት ቀርበዉ እንዲመዘገቡ ወላጆች የሚጠበቅባቸዉን ኃላፊነት እንዲወጡ ጥሪ ቀረበ
ሀዋሳ፡ ነሐሴ 16/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) የካፋ ዞን ትምህርት መምሪያ ለ2018 የትምህርት ዘመን ተማሪዎች በወቅቱ ትምህርት ቤት ቀርበዉ እንዲመዘገቡ ወላጆች የሚጠበቅባቸዉን ኃላፊነት እንዲወጡ አሳስቧል።
በአዲሱ የትምህርት ዘመን ከ350 ሺህ በላይ ተማሪዎችን ለመመዝገብ ዝግጅት ማድረጉንም መምሪያዉ አስታዉቋል።
የመምሪያ ኃላፊ አቶ ሙሉጌታ መሸሻ በደቡብ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት ከቦንጋ ጣቢያችን ጋር ባደረጉት ቆይታ፥ በሁሉም አካባቢዎች የ2018 ትምህርት ዘመን ስራ ለማስጀመር የሚያስችል ቅድመ ዝግጅት በማጠናቀቅ ተማሪዎችን ለምዝገባ እየተጠባበቅን ነዉ ብለዋል።
በዞኑ ከቅድመ መደበኛ ጀምሮ በሚገኙ 643 ትምህርት ቤቶች 351 ሺህ 458 ተማሪዎችን በመመዝገብ የ2018 ትምህርት ዘመን የመማር ማስተማር ስራ ለመጀመር የሚያስችሉ ስራዎች መጠናቀቃቸዉንም አንስተዋል።
በዚህም ምዝገባ ከነሐሴ 19/2017 ጀምሮ ለአምስት ተከታታይ ቀናት እንደሚከናወን ገልጸዉ፤ ወላጆች ልጆቻቸዉን በጊዜ ወደ ትምህርት ቤት በመላክ እንዲያስመዘግቡም ጥሪ አስተላልፈዋል።
በዞኑ በፓይለት ደረጃ በተመረጡ ወረዳዎችና ከተማ አስተዳድሮች የአንድ ቀን ምዝገባ ስራ ነሐሴ 16/2017 ዓ/ም በይፋ መጀመሩንም አቶ ሙሉጌታ ገልጸዋል።
የመማር ማስተማር ስራዉ ስኬታማ መሆን እንዲችልም በክረምት ወቅት የመማሪያ ክፍሎችን ማሟላት፣ የትምህርት ቤት ግብአቶችንና የግቢ ማጽዳትና መሰል እንቅስቃዎች እየተከናወኑ መቆየታቸዉን ጠቁመዋል።
ዘጋቢ፡ በአሰግድ ሣህሌ – ከቦንጋ ጣቢያችን

More Stories
የእናቶችንና ጨቅላ ህፃናትን ሞት ለመቀነስ በሚደረጉ ጥረቶች ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ ተገለፀ
የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርእሰ መስተዳደር (ዶ/ር ) እንዳሻው ጣሰው በተገኙበት በጉራጌ ዞን ወልቂጤ ከተማ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ምርቃትና የመሰረተ ድንጋይ የማስቀመጥ ስነ-ስረዓት እየተካሄደ ይገኛል
በጎፋ ዞን ሳውላ ከተማ የምግብ ዋስትና ፕሮጀክት እየተስተዋለ ያለውን ድህነት እና የስራ አጥነት ችግር ለመቅረፍ ያበረከተው አስተዋጽኦ የላቀ መሆኑ ተገለጸ