ሴቶች የኢኮኖሚ አቅማቸውን እንዲያሳድጉ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑን የቦረዳ ወረዳ ሴቶችና ህፃናት ጽ/ቤት አስታወቀ
ሀዋሳ፡ ነሐሴ 13/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) በጋሞ ዞን የቦረዳ ወረዳ ሴቶችና ህፃናት ጽ/ቤት ሴቶች የኢኮኖሚ አቅማቸውን እንዲያሳድጉ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑን አስታውቋል፡፡
ወ/ሮ ካሰች ክብረት ሥራው ድንቅ የማገዶ ቆጣቢ ምድጃ አምራች ማህበር ሰብሳቢ ሲሆኑ የደን ጭፍጨፋን ለመቀነስ እንዲቻል ጂ.አይ.ዜድ የተሰኘ ድርጅት በማገዶ ቁጠባ ምድጃ ዙሪያ በሀላባ ስልጠና እንዲወስዱ ማድረጋቸውን ጠቁመዋል።
ቪታ የተሰኘ ድርጅት ከ2015 ዓ.ም ጀምሮ የገበያ ትስስር መፍጠር በመቻሉ ለተለያዩ የዞኑ ወረዳዎች እያቀረብን እንገኛለን ያሉት የማህበሩ ሰብሳቢ ወ/ሮ ካሠች፥ 15 ሺህ 300 ማገዶ ቆጣቢ ምድጃ ለገበያ ማቅረብ በመቻላቸው ከ6 ሚሊየን 850 ሺህ ብር ካፒታል እንዲያገኙ አመላክተዋል።
ማህበሩ አስር ለሚሆኑ ሥራ አጦች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉንም ሰብሳቢዋ ተናግረዋል።
ወ/ሮ ዘመቱ ተሾመ የማህበሩ አባል በመሆናቸውና ወደ ሥራ በመግባታቸው የወንድን እጅ ከመጠበቅ እንዳዳናቸው አስረድተው ከሚያገኙት ገቢ ፍየል ገዝተው እያረቡ መሆናቸውን ተናግረዋል።
ሌላኛዋ የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ወ/ሮ ጤና አበራ በየቤቱ በመሄድ ምድጃውን መገጣጠም በመቻላቸው ተጠቃሚ እንደሆኑ አስረድተዋል።
የቦረዳ ወረዳ ሴቶችና ህፃናት ጽ/ቤት ኃላፊ ወ/ሮ አማረች አይዛ ሴቶች የኢኮኖሚ ባለቤት እንዲሆኑ ሥራዎች በትኩረት እየተሰራ መሆናቸውን ተናግረዋል።
ሴቶች በማህበር ተደራጅተው ቁጠባ ላይ ትኩረት እንዲያደርጉ ይደረጋል ያሉት ኃላፊዋ ከማገዶ ቆጣቢ ምድጃ ማህበር በተጨማሪ በጓሮ አትክልትና በዶሮ እርባታ ላይ እንዲያተኩሩ ይደረጋል ነው ያሉት።
በቦረዳ ወረዳ ሴቶችና ህፃናት ጉዳይ ጽ/ቤት የሴቶች ንቅናቄ ተሣትፎ ዳይሬክቶሬት ቡድን መሪ አቶ ኢሳያስ ኮይራእ በወረዳው ባሉ 31 ቀበሌያት የሚገኙ 17 ሺህ 586 ሥራ አጥ ሴቶች በማህር በመደራጀት በገቢ ማስገኛ ሥራ እንዲሰማሩ ተደርጓል።
ለአብነትም በማገዶ ቆጣቢ ምድጃ የተደራጁ ሴቶች ወደ አጎራባች ዞኖችም ጭምር ምርታቸውን እንዲያቀርቡ በመደረጉ ተጠቃሚ መሆናቸውን አመላክተዋል።
ዘጋቢ ፡ ታምሩ በልሁ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን

More Stories
በ6 ወራት ውስጥ ሊመዘበር የነበረ ከ156 ሚሊየን 560ሺህ ብር በላይ ማዳን መቻሉ ተገለጸ
የጉራጌ ክትፎ ባህልና እውቀትን በዩኒስኮ የሰው ልጆች ወካይ የማይዳሰስ ቅርስነት ለማስመዝገብ እየተሰራ እንደሚገኝ የኢፌዲሪ ቅርስ ባለስልጣን ገለፀ
በክልሉ ያሉ ብሔረሰቦችን ባህል ወደፊት በማውጣት የአካባቢውን ሰላምና ልማት ለማስቀጠል በትኩረት መስራት እንደሚገባ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳደር ኢንጅነር ነጋሽ ዋጌሾ(ዶ/ር) ተናገሩ